ሰንሰለታማ ተራራዎችን ተንተርሳ፤ አስደናቂ መልከዓምድር ላይ ትገኛለች ጩጊ ማርያም። ቦታው የተባረከ፤ ሰንሰለቱ የተጋመደ እና አካባቢው አረንጓዴ ሸማን የለበሰ ነው። በአማራ ክልል ማዕከላዊ ጎንደር ዞን ወገራ ወረዳ ከሚገኙ ጥንታዊ ገዳማት መካካልም ጩጊ ማርያም ወአቡነ ምዕመነ ድንግል አንድነት ገዳም አንዷ ናት። ገዳሟ ከጎንደር ከተማ 37 ኪሎ ሜትር ርቀት እንዲሁም ከኮሶዬ ከ2 ሰዓት የእግር ጉዞ በኋላ ጉንዳ ጩጊ ቀበሌ ላይ ትገኛለች።
በወገራ ወረዳ ባሕል፣ ቱሪዝም እና ስፖርት ጽሕፈት ቤት የቅርስ ጥበቃ እና እንክብካቤ ቡድን መሪ እንዳልክ ተቀባ ጩጊ ማርያም ወአቡነ ምዕመነ ድንግል አንድነት ገዳም በ1 ሺህ 632 ዓ.ም በአጼ ፋሲል ዘመን መንግሥት አባ ምዕመነ ድንግል በተባሉ አባት እንደተመሠረተች የታሪክ ድርሳናት ጠቅሰው ያብራራሉ። ገዳሟ በርካታ ቋሚ እና ተንቀሳቃሽ ቅርሶች ባለቤትም ናት።
በጩጊ ማርያም ጥንታዊ የብራና መጻሕፍት፣ ጥንታዊ መስቀሎች፣ የዮርዳኖስ ጸበል (ማይ ዮርዳኖስ) ጠጥተው አጽማቸው ያልፈረሱ ከ400 ዓመት በላይ የቆዩ የ16 ፍየሎች አጽም፣ ወድቆ የተነሳ ችብሃ ዛፍ፣ የኢትዮጵያ ካርታ ቅርጽ ያለው ዋሻ እና ሌሎችም ድንቅ መስህቦች ይገኛሉ፡፡
በገዳሙ ውስጥ በውል የማይታወቅ ምስጢራዊ ዋሻ መኖሩንም ነው የተናገሩት ።
በዋሻው ውስጥ የሚገኘው የዮርዳኖስ ጸበል (ማይ ዮርዳኖስ) አይፈስም፣ መጠኑም አይጨምርም፣ አይቀንስም በአንድ ቦታ የቆመ ጥርት ያለ መኾኑ ደግሞ ድንቅ የተፈጥሮ ገጽታውን ይገልጻል።
ከዚህ ፀበል የተንሳፈፈ ተዓምራዊ ድንጋይ እንደሚገኝ አባቶች እንደሚያስረዱም ነው የገለጹት። በዮርዳኖስ ጸበል (ማይ ዮርዳኖስ) ካህናት ብቻ እንደሚገቡ እና አማኞችም ፈውስ እንደሚያገኙበት ነው የጠቆሙት።
ለገዳሙ የተሰጠው ቃል ኪዳን ጸበሉን የጠጣ አካሉ ሳይፈርስ ለረጅም ዘመን እንደሚቆይ የገዳሙን የታሪክ ድርሳናት ዋቢ በማድረግ ተዓምራዊ ገጽታውን ያስረዳሉ። በቦታው ብዙ የቅዱሳን አባቶች አጽም ሳይፈርስ እንደሚገኝም ነው የገለጹት። በርካታ ተፈጥሯዊ ዋሻዎችም በአካባቢው ይገኛሉ። በተራራዎች መካከል “ሰቋር” የተባለ የተፈጥሮ ድልድይ ይገኝበታልም በማለት ያለውን ድንቅ ተፈጥሮ ነግረውናል።
በዙሪያዋ ለዐይን የሚስቡ ሰንሰለታማ ተራራዎች እና አዕምሮ የሚያድሱ እና ልቦናን በሀሴት የሚሞሉ ሀገር በቀል ዛፎች መኖራቸውንም ነው ያስረዱት። ከገዳሟ ታሪካዊ እና ሃይማኖታዊ መስህቦች በተጨማሪ እጅግ አስደማሚ የተራራ ሰንሰለቶች እና አስደናቂ የመልክዓ ምድር ውበቶችን ለማየት ዕድል የሚሰጥ ልዩ ሥፍራም ነው።
ቡድን መሪው እንደተናገሩት ቦታውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ፣ ለማልማት እና ለማስተዋወቅ የተለያዩ ተግባራት መሠራቱን ገልጸዋል። የገዳሟ የንግሥ በዓልም በየዓመቱ ጳጉሜ 3፣ ጥር 21 እና ሰኔ 21 እንደሚከበርም ነው የተመላከተው።
በሥራውድንቅ ደሳለው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!









