አማራ ክልልን ቀዳሚ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እየተሠራ ነው።

0
31
ባሕር ዳር: ሚያዝያ 26/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ኢትዮጵያ በርካታ የሚዳሰሱ እና የማይዳሰሱ ቅርሶችን በዩኔስኮ በማስመዝገብ በአፍሪካ ቀዳሚ ሀገር ናት።
ባለፉት ዓመታት ደግሞ ከቀደምቶቹ የቱሪዝም መዳረሻዎች ባሻገር አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎች ተገንብተዋል። የቱሪዝም መነቃቃትም ተፈጥሯል።
✍️ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ከዓመታት በፊት፦
👉 የቱሪዝም ዘርፉ ከቅርስነት ያልተሻገረ፤ በነባር ታሪካዊ ሥፍራዎች እና ቅርሶች ላይ የተንጠለጠለ ነበር።
👉 የመሠረተ ልማት ክፍተቶች፦ ነባሩ መዳረሻዎች በቂ ማረፊያ ሆቴሎች እና ሎጅዎች የሌላቸው፣ የመንገድ፣ የኃይል እና መሰል አቅርቦቶች ያልተሟሉላቸው ነበሩ።
👉 የኢኮኖሚ አበርክቶው ደካማ ነበር። በዘርፉ እምቅ አቅም ቢኖርም የሚገኘው ገቢ ለሀገር ኢኮኖሚ እድገት የነበረው አበርክቶ ዝቅተኛ ነበር። ይሁንና ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የቱሪዝም ዘርፉ ትኩረት እየተሠጠው ይገኛል።
ከዓመታት ወዲህ ግን ለቱሪዝም በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም ተጠቃሚነት እያደረገ መጥቷል።
✍️ ባለፉት ዓመታት የአማራ ክልል የቱሪዝም ተጠቃሚነት፦
👉 እንደ ጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት፤ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት እና የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርትን የመሳሰሉ አዳዲስ መዳረሻዎች ተፈጥረዋል።
👉 የቅርሶች ጥገና እና የመሠረተ ልማት ዝርጋታ ተከናውኗል።
👉 የጎብኝዎች ቁጥር እንዲጨምር እና የቆይታ ጊዜያቸው እንዲራዘም ዕድሎች ተፈጥረዋል።
👉 ከዘርፉ የሚገኘው ገቢ እንዲጨምር አድርጓል።
👉 ዘርፉ ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ ነው። የአማራ ክልል ባሕል፣ ቱሪዝም እና ስፖርት ቢሮ ኀላፊ መልካሙ ጸጋየ ከአሚኮ ጋር በነበራቸው ቆይታ የክልሉን ቱሪዝም ለማነቃቃት ጠንካራ ሥራዎች ተከናውነዋል ነው ያሉት።
በተለይም የክልሉ ሰላም መሻሻል በዘርፉ ላይ የልማት ሥራዎች እንዲከናወኑ እና ዓለም አቀፍ ጎብኝዎች ወደ ክልሉ እንዲመጡ ዕድል ፈጥሯል ነው ያሉት።
በበጀት ዓመቱ ባለፉት ወራት ከቱሪዝም ዘርፍ 16 ቢሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል ብለዋል። ከ152 ሺህ በላይ የሚኾኑ ዜጎች በዘርፉ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እንደኾኑም ገልጸዋል። ይህም የቱሪዝሙን መነቃቃት ያሳያል ነው ያሉት።
ይህ ተስፋ የተጣለበት የቱሪዝም ዘርፍ በአማራ ክልል መንግሥት የ25 ዓመት አሻጋሪ እድገት እና ዘላቂ ልማት ዕቅድ ትኩረት ተሰጥቶታል ብለዋል።
በዘርፉ ያለውን እምቅ አቅም በማልማት ክልሉን ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ የማድረግ ግብ አንግቦ ወደ ሥራ ገብቷልም ብለዋል።
ዘጋቢ፦ አድኖ ማርቆስ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here