ሎካ አባያ ብሔራዊ ፓርክ

0
248

በደቡብ ኢትዮጵያ ሲዳማ ክልል አባያ ወረዳ ይገኛል፤ ሎካ አባያ ብሔራዊ ፓርክ:: ብሔራዊ ፓርኩ ከሀዋሳ 68 ከአዲስ አበባ ደግሞ 343 ኪሎ ሜትር ይርቃል።

በኢትዮጵያ ስምጥ ሸለቆ ውስጥ የሚካተተው ፓርኩ በ2000 ዓ.ም ሲከለል 500 ኪሎ ሜትር ስኩዌር  ተለክቷል:: በመልካምድራዊ አቀማመጡ  ኮረብታማ፣ የሳር ሜዳ፣ ረግረጋማ፣ ገደላማ፣ ሐይቅ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ ደንና ሸለቆዎችን ያካተተ ነው::

የፓርኩ ክልል ዝቅተኛው ሻላ ኦዳ ከመሬት ወለል አንድ ሺህ 178 ሜትር ከፍታ፣ ከፍተኛው የጉዳኖ ኮረብታ አንድ ሺህ 650 ሜትር ተለክቷል::

በፓርኩ 198 የእጽዋት ዝርያዎች ተመዝግበዋል::

የፓርኩ ክልል በረሀማ እና ወይና ደጋ የዓየር ንብረት አለው፤ አማካይ የሙቀት መጠኑ 16 ዲግሪ ሴንቲ  ግሬድ ተለክቷል:: ሁለት የዝናብ ወቅቶች አሉት።  ወራቶቹም የመጀመሪያው ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዚያ ወር መጨረሻ፣ ሁለተኛው ደግሞ ከሀምሌ እስከ ጥቅምት ናቸው።

ዓመታዊ የዝናብ መጠኑ ዝቅተኛው 374 ፤ ከፍተኛ 1 ሺህ 194 ሚሊ ሜትር ሲሆን ከ2004 እስከ 2017 እ.አ.አ አማካይ የዝናብ መጠን 846 ሚሊ ሜትር ተለክቷል::

በፓርኩ ውስጥ ለሚገኝ ብዝሃ ህይወት የአባያ ኃይቅ እና የብላቴ ወንዝ ዋነኛ መሠረት ናቸው:: በፓርኩ ክልል በ28 መካከለኛ እና ትልልቅ የዱር እንስሳት ዝርያዎች ውስጥ የሚካተቱ በቁጥር 2 ሺህ 573 እንደተጠለሉ ተለይቷል:: ከተጠቀሱት 28 ዝርያዎች የአፍሪካ የዱር ውሻ፣ ነብር እና ጉማሬ ሊጠፉ ከተቃረቡት ውስጥ እንደሚካተቱ በድረ ገጹ ተመላክቷል::

በፓርኩ ክልል ተበራክተው ወይም በቁጥር ላቅ ብለው ከሚገኙ የዱር አንስሳት ዝንጀሮ እና የሜዳ ፍየል በቅደም ተከተል ተጠቅሰዋል::

በመረጃ ምንጭነት ሪሰርች ጌት እና ቪዚት ሲዳማ ድረገፆችን  ተጠቅመናል::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር መጋቢት 30 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here