ሙት ባሕር፣ አል- በሀር፣ አል – ሜይት፣ ጨው ባሕር ወ.ዘ.ተ ተብሎ ይጠራል:: ሙት ባሕር በደቡብ ምእራብ እስያ በደቡብ እስራኤል ዮርዳኖስን በምትዋሰንበት ምስራቃዊ ቀጣና ነው የሚገኘው:: ቀጣናው አራት ሚሊዬን ዓመታት ካስቆጠሩ ጨዋማ ዝቅተኛ ቦታዎች አንዱ ነው:: ሙት ባሕር በረሀማ ፣ ከፍተኛ ሙቀት እና አነስተኛ ዝናብ የሚጥልበት ነገር ግን ውኃው በልዩ የማእድን ይዘቱ ለተለያዩ የቆዳ በሽታዎች ፈውስ የሚመረጥ መሆኑን ድረ ገፆች አስነብበዋል::
ቀደም ብሎ ወደ ሙት ባሕር የሚፈስ የዮርዳናስ ወንዝ ብቻ ነበር:: አሁን ላይ ግን ከዙሪያው አስተኛ መጠን ያላቸው ምንጮች ብቻ ናቸው ያሉት:: በባህሩ ወለል የሚታየው ጨው ወይም አብረቅራቂ “ሶዲዬም ክሎራይድ” ብቻ ነው:: የባሕሩ ሰሜናዊ ዳርቻ በጭቃ ደቡባዊው ደግሞ በጨው ስብርባሪ የተሞላ ነው::
የባሕሩ መገኛ ከባህር ወለል ከ400 እስከ 430 ሜትር ጥልቀት ላይ እንደሚገኝ ተለክቷል:: በየዓመቱ አንድ ሜትር ቁልቁል እንደሚቀንስም ነው ድረ ገፆች ያስነበቡት::
ሙት ባሕር ሙት የተባለበት ምክንያት በጨዋማነቱ፣ ለእፅዋትም ሆነ ለእንስሳት የማይመች በመሆኑ ነው:: ይሁን እንጂ አንስተኛ መጠን ያላቸው ተህዋስያን እና ፈንገሶች ይገኛሉ::
የሙት ባሕር ወለል በቀጣናው አነስተኛ መጠንም ቢሆን ዝናብ በሚጥልበት ወቅት ወለሉ ደማቅ ቀይ ቀለም ይላበሳል- ያም ልዩ ዓይነት አልጌ መላበሱን አመላካች ነው::
በሙት ባህር በቆዳ ላይ የሚወጡ በሽታዎች እና የቀለም ችግር መድሃኒት የሆኑ ማእድናት ይገኛሉ:: በቀጣናው የኦክስጂን መጠን ከፍ ያለ በመሆኑም አካልን ለማደስ ይመረጣል፣ እናም ሰዎች ይዋኙበታል በውስጡ ይዘፈዘፋሉም:: ውኃው ግን ያንሳፍፋል እንጂ አያሰጥምም::
ሙት ባህር መስህብ የሚሆኑ ጠመዝማዛ መንገዶችን፣ ድብቅ ፏፏቴዎችን፣ ምንጮች እና ዋሻዎችንም ይዟል::
በ1955 እ.አ.አ የ”ፖታሽ” እና “የማግኒዚዬም እና ክሎራይድ” ፋብሪካ ተከፍቷል:: በደቡባዊ ዮርዳኖስ የኬሚካል ማቀነባበሪያ ተቋማትም ይገኛሉ::
ለዘገባችን በመረጃ ምንጭነት ፋይንድ ሎስት፣ ትራቭል ቶክቱር እና ዴድ ሲ ድረ ገፆችን ተጠቅመናል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የሰኔ 2 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም