በበቀቀን የተወረረችው ከተማ

0
154

በአርጀንቲና ከቦነስአይረስ በስተደቡብ የምትገኘው ሂላሪዮ አስካሱቢ ከተማ በሺህ በሚቆጠሩ የዱር በቀቀኖች በመወረሯ በጩኽታቸውም ሆነ መሰረተ ልማት ላይ በሚያደርሱት ጥፋት ኗሪዎች መማረራቸውን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ አስነብቧል::

ኗሪዎች ከተማዋ ቀደም ባሉት ዓመታት ጀምሮ በበቀቀኖች መንጋ ብትወረርም ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ግን  እየተበራከቱ የሚያደርሱት ጥፋትም ሆነ የድምፅ ብክለት እያየለ መምጣቱን ነው በምሬት የገለጹት:: የበቀቀኖቹ መንጋ ቁጥራቸው እየተበራከተ በመሄዱ በቋሚ ምሰሶ ላይ የተዘረጉ የስልክ፣ የበየነ መረብ፣ የኤሌክትሪክ ገመዶችን  በመንከስ እና በመቆራረጥ ለኪሳራ መዳረጋቸው ነው የተብራራው::

በየጐዳናዎች እና ዳርቻዎች በቀቀኖቹ የሚጥሉት ኩስ ከተማዋን አጉድፎ ከማስቸገሩም ባሻገር ሌት ተቀን የሚያሰሙት የማያቋርጥ ጩኽት ኗሪዎቹን ማወኩ ነው በእማኞች  የተጠቀሰው::

አምስት ሺህ የሚደርሱት የሂላሪዮ አስካሱቢ ኗሪዎች ከአእዋፉ ጋር አብረው መኖር እንደማይችሉ ቢያስታውቁም የከተማዋ አመራሮች ምንም ማድረግ እንደማይችሉ ነው ምላሽ የሰጡት::

በከተማዋ የተስተዋለው በበቀቀኖች የሚደርሰው ችግር አዲስ አለመሆኑን እና ባለስልጣናቱ ችግሩን ለማቃለል ቢጥሩም ምንም ማድረግ አለመቻላቸው ተጠቁሟል:: በባለስልጣናቱ ከተሞክሩ የችግር ማቅለያዎች አእዋፉን ማባረሪያ ድምፆች ማሰማት፣ የተለያዩ ቀለማት ያላቸው መብራቶችን (laser light) መልቀቅ ይገኙበታል:: በመከላከያ ወይም በማራቂያነት ቢተሞከሩት ድምፅና ቀለማትን የሚፈነጥቅ ብርሃን በመጀመሪያው ጊዜ ቢሸሹም በሂደት እየተላመዱት ሁከታቸው መቀጠሉ ነው የተገለፀው::

የግብርና ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ፓኦሎ ሳንቼዝ አንሳኖቫ ከ2013 እ.አ.አ ጀምረው በከተሞች የዱር በቀቀኖች ብዛታቸው ለመጨመሩ  መነሻው ምን እንደሆነ አጥንተዋል:: በጥናታቸውም ሰዎች በበቀቀኖቹ ተፈጥሯዊ መኖሪያ ደን ላይ ባደረሱት ጭፍጨፋ እና ምንጣሮ መሰደዳቸውን አረጋግጠዋል::

የዱር በቀቀኖች በአርጀንቲና ጥበቃ ስለሚደረግላቸው በአእዋፉ ላይ የሚወሰድ ጉዳት የሚያደርስ ርምጃ በጥብቅ በመከልከሉ ከመታገስ ውጪ አማራጭ መፍትሄ አለመኖሩ ነው በማደማደሚያነት የሰፈረው::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር ጥቅምት 18  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here