በንግግር የሰላም በር ይከፈት!

0
206

በተራዘመ ጦርነት፣ ጊዜ በወሰደና ቶሎ ባልተፈታ ግጭትና ብጥብጥ ውስጥ ሞት፣ አካል
መጉደል፣ መፈናቀልና ስደት ሁልጊዜም አሉ:: ከዚህ በተረፉት ደግሞ አካላዊ፣ ስነልቦናዊና
ቁሳዊ እንዲሀም ቋሚና ጊዜያዊ ጉዳትን አስከትሎ ያልፋል::
ከነዚህ ዘርፈ ብዙ ጉዳቶች መካከል የትምህርት መቋረጥ አንዱ ነው:: በተለይም እንደኛ
ባለ ታዳጊ ሀገር ትምህርት የችግር ሁሉ መፍቻ፣ የዕድገት መሰረትና መውጫ መንገድ ነው::
በጦርነት ምክንያት ብዙ ሕጻናት መደበኛ ትምህርታቸውን መከታተል ያቆማሉ::
አንዳንዶቹ ከመኖሪያ ቀያቸው ይፈናቀላሉ:: በአካቢያቸው የቀሩት ደግሞ ከዛሬ ነገ ምን
ይፈጠራል በሚል ስጋት ውስጥ ይኖራሉ:: በትምህርት የመለወጥ ተስፋና ራዕይ የነበራቸው
ባለብዙ ሕልም፣ ችግር ፈችና መፍትሔ አፍላቂ ጭንቅላት ባለቤቶች ሁሉ የትም ተበትነው
በምን ይሆናል ስጋት ከነሕልማቸው በተስፋ መቁረጥ እንዲቀመጡ ምክንያት ሆኗል::
ምንም እንኳን በዓለም አቀፍ የጦር ሕግ ትምህርት ቤቶችና የሃይማኖት ተቋማት
ከጦርነት ኢላማነት የሚከለክል ህግ ቢኖርም ብዙ ትምህርት ቤቶች ፈርሰዋል፤ አብዛኞቹ
ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው አልተመለሱም:: የመጡትም ከፍርሃትና ከስጋት ነጻ
ሆኖ የመማር ስነልቦናዊ ዝግጅት አይኖራቸውም::
በጦርነትና በግጭት መሃል የሚያልፉ ሕጻናት የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውንም
ለመጨረስ አልቻሉም::
በተለያየ ጊዜ በተለያየ ምክንያት የትምህርት መቋረጥ በትምህርት የሚገኘውን ዘርፈ ብዙ
ጥቅም ያሳጣል:: በጤና፣ በኢኮኖሚያዊና በፍትሀዊ ተጠቃሚነት፣ በማህበራዊ ደህንነትና
በዓዕምሮ ጤና መስክ የሚኖረውን እኩል ተጠቃሚነትና እድል በማሳጣት ለድህነትና
ለጉስቁልና የሚያጋልጥ ጉዳት አድርሶ ያልፋል::
በተለይም በአማራ ክልል ባለፉት ሶስት ዓመታት ጀምሮ ክልሉ ውስጥ በነበረው ጦርነትና
አሁንም ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያት መደበኛ የመማር ማስተማር ሂደት ተስተጓጉሏል::
በግጭት ውስጥ ተማሪዎችን ፍርሃት፣ ስጋትና ቀጥሎ ስለሚከሰተው ነገር እርግጠኛ
አለመሆንና ተስፋ መቁረጥ ይጫናቸዋል:: ይህንን ስሜት ተቋቁመው በሚማሩትም ላይ
ቢሆን ውጤታማነታቸውን በመፈተን የጦርነቱና የግጭቱ ጠባሳ ጫና ያሳድርባቸዋል::
ይህንን ስሜት ለማከምም የስነልቦና ህክምናና እርዳታ ያስፈልጋቸዋል::
በጦርነትና በግጭት ከሚደርሰው ዘርፈ ብዙ ችግር የሁሉም የስራ መስኮች የጀርባ
አጥንት የሆነው አንዱ የትምህርት ዘርፍ በዚህ መልክ መጎዳት ለሁለም መስክ መጎዳት፣
ለትውልድም ብሩህ እጣ ፋንታ መጨለም ነው:: በተለይም በተራዘመ ጦርነትና ግጭት ብዙ
ዋጋ የከፈሉ ሀገራት ስለሰላም አብዝተው የሚሰብኩት የህመሙን ክብደት በማየታቸው
ነው:: በርግጥስ የሰላምን ዋጋ ለመመዘንና ዋጋ ለመስጠት ምን ያህል ህይወት መስዋእት
ሲሆን ነው የሚገባን? ለውይይትና ለንግግር በር የዘጋ ልቦና ይዘን ሰላምን ለማምጣት
ከጦርት መማርን እንዴት መረጥን? አሁንም በንግግር የሰላም በር ይከፈት!

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here