በቻይና የመንገድ እና ትራንስፖርት አገልግሎት ባለስልጣን የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች በጉዞ ላይ እንዳያሸልቡ እና አደጋ እንዳይፈጠር ለመከላከል ባለቀም ጨረር የሚፈነጥቁ መብራቶችን በማንቂያነት ለመገልግል በሙከራ ላይ መሆኑን ኦዲት ሴንትራል ድረ ገጽ አስነብቧል፡፡
ባለፈው የአውሮፓውያኑ 2023 ሙከራው የጀመረው የአሽከርካሪዎች ማንቂያ – በቀለማት ያሸበረቀው የብርሃን ጨረር በርካታ አስተያየቶች ተሰንዝረውበታል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ ከፊሎቹ በፍጥነት ማሽከርከሪያ ጐዳናው በረዢም ርቀት ላይ የተተከለው ባለ ቀለም የመብራት ጨረር የአሽከርካሪዎችን ትኩረት ይከፋፍላል የሚል ግብረ መልስ ሰጥተዋል፡፡
በሌላ በኩል ከፊሎቹ ረዢም ርቀት ሲያሽከረክር የነበረን ሰው ድካሙን ለመቀነስ፣ ማሸለብን፣ መዘናጋትን ለመግታት እንደሚያስችል በማህበራዊ ድረ ገጽ ምላሻቸውን አስነብበዋል፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት ከማንቃት ይልቅ ሌላ ችግር ይፈጥራል ከሚሉት ወገን አስተያየታቸውን ካሰፈሩቱ “ባለቀለም መብራቱ የሚጥል ህመም ያለባቸውን ህመማቸውን ይቀሰቅሳል፤ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል” የሚል አስተያየት ነው የሰጡት፡፡
ባለስልጣናቱ አደጋን ለመቀነስ ያስችላል፣ አሽከርካሪዎችን ያነቃል ብለው የጀመሩት ባለቀለም የብርሃን ጨረር ትኩረትን እንደሚከፋፍል እና በአሽከርካሪዎች እየተለመደ ሲሄድ ትኩረትን እንደሚከፋፍል እና እየተለመደ ሲሄድ ከማንቃት ይልቅ ማንቀላፋትን ሊያሰፍን እንደሚችልም ነው ያሰመሩበት- አስተያየት ሰጪዎቹ፡፡
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር ነሐሴ 13 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም