ከስድስተኛ ፎቅ የወደቁት አዛውንት

0
102

በሩሲያ ከተሪንበርግ ከተማ ኗሪዋ የ80 ዓመት አዛውንት ከጋራ መኖሪያ ህንፃቸው ስድስተኛ ፎቅ  መስኮት ወድቀው ቢወረወሩም ከስር በቆመ ተሽከርካሪ አናት ላይ በማረፋቸው በህይወት መትረፋቸውን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ ባለፈው ሳምንት አስነብቧል::

አደጋው የደረሰው አዛውንቷ የመኖሪያ ክፍላቸውን መስታውት ውጪያዊ ገጽ እያፀዱ በነበረበት ወቅት ነው:: አስደንጋጩ አደጋ በህንፃው ላይ በተገጠመ  የደህንነት መከታተያ ካሜራ የተቀረፀ ሲሆን ሁነቱ በማህበራዊ ድረ ገፆች በመለቀቁም እጅግ በርካታ ተከታታዮች ተመልክተውታል::

ድረ ገጹ እንዳስነበበው አዛውንቷ ከስድስተኛ ፎቅ ቁልቁል ተወርውረው  በታችኛው ወለል ላይ በቆመች የጐረቤት ተሽከርካሪ ጣሪያ ላይ ካረፉ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ምንም ጉዳት ሳይደርስባቸው በእግራቸው መራመድ ችለዋል::

አዛውንቷ ጐረቤታቸውን ጠርተው አብረው በአቅራቢያው ወደሚገኝ የጤና ተቋም ሄደው በመመርመር ደህንነታቸውን ማረጋገጥ መቻላቸውም ነው የተገለፀው::

በሩሲያ “ኢ1 አርዩ” የተሰኘ መገናኛ ብዙሃን አዛውንቷ በራሳቸው ቸልተኝነት ወይም የጥንቃቄ ጉድለት መውደቃቸውን ነው የዘገበው:: የቀጣናው የፓሊስ ጽ/ቤት ባልደረቦችም በቦታው ተገኝተው የተለያዩ መረጃዎችን ሰብስበዋል፤ ምርመራ ባካሄዱበት የጤና ተቋምም ባለሙያዎችን ጠይቀው ምንም ዓይነት ጉዳት ሌላው ቀርቶ በአካላቸው ላይ ጭረትም እንዳልደረሰባቸው ነው ያረጋገጡት::

ከአዛውንቷ ይልቅ ያረፉበት የተሽከርካሪዋ ጣሪይ ጐድጐድ ማለቱን  ብቻ ነው በፎቶግራፍ አንስተው ለእይታ ያበቁት::

በመጨረሻም ፓሊስ በሰጠው የመጀመሪያ ደረጃ የምርመራ ሪፖርት አዛውንቷ በግዴለሽነት መውደቃቸውን ጠቅሶ ተጨማሪ ማስረጃ እና የተለየ መንስኤ መኖር አለመኖሩን ለመገንዘብ የማጣራት ስራው መቀጠሉን ነው በማደማደሚያነት ያሰፈረው::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር የሚያዝያ 27 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here