“ከብት ርባታ ለሠራ  ዋጋ ይከፍላል”

0
59

በባሕር ዳር ከተማ የሚገኘውን  አዲሱን የዓባይ ድልድይ ተከትሎ ወደ አየር ጤና በሚያስኬደው  የአስፋልት ዳር በግራ በኩል ሰፋፊ የከብቶች ቤት ይታያል:: ከዋናው አስፋልት እና በፎቆች መካከል በሚገኘው በዚህ ቦታ በጥቃቅን እና አነስተኛ ተደራጅተው ከብቶችን የሚያረቡ ሰዎች የሚሠሩበት አካባቢ ነው::

እኛም ከሰሞኑ በወተት ሀብት ከተሰማሩት ወ/ሮ ብዙሀረግ ታደሰ ጋር ቀጠሮ ስለነበረን ወደዚሁ ቦታ አቅንተን ነበር:: ከወይዘሮ ብዙሀረግ የሥራ ቦታ እንደደረስንም ወቅቱ የክረምቱ መግቢያ በመሆኑ  የእነሱም ሆነ የከብቶች መውጫ እና መግቢያ ውኃ እንዳያቁርና ጭቃ እንዳይሆን  ሲደለድሉ፤ ጣራው ላይ ካለው ቆርቆሮ የሚያፈስ እንዳለው በባለሙያ ሲያስፈትሹ አገኘናቸው::

ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ እያከናወኑት ስላለው ሥራ፤ “ካሉኝ ከብቶች አብዛኞቹ የወተት ላሞች ናቸው::  በክረምት  ርጥበት ከተሰማቸው ደግሞ ጡታቸው ስለሚቆስል የተሻለ መቆሚያ፣ መውጫ መግቢያ እንዲሁም መተኛ ቦታ ስለሚያስፈልጋቸው ያን እያደረግን ነው” በማለት ገለጹልን:: ግቢውን በዐይናችን ስናማትር የጥጆች ማቆያ፣  የከብቶች የሳር መከመሪያ፣ ማደሪያ እና መመገቢያቸው  ለየብቻ ተሠርቶ ተመለከትን::

በባሕር ዳር ዙሪያ የተወለዱት ወይዘሮ  ብዙሀረግ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁት  በባሕር ዳር ከተማ ነው:: ወይዘሮዋ  በ1982 ዓ.ም የተሻለ ኑሩ  ፍለጋ ወደ አረብ ሀገራት በመሄድ  ለሁለት ዓመት በሥራ ቆይተዋል:: በኋላ ወደ ሀገራቸው በመመለስ  በጊቤ የኀይል ማመንጫ በወጥ ቤት ሠራተኝነት ተቀጠሩ::   በዚህ  የሕይወት አጋጣሚ ከልጆቻቸው  አባት ጋር በመተዋወቅ ትዳር መሰረቱ::

ወይዘሮዋ በትዳራቸው ሦስት ልጆችን ለማፍራት ቢታደሉም በ2003 ዓ.ም ባለቤታቸውን ሞት ነጠቃቸው:: በወቅቱ ከሀዘኑ ጋር ልጆቻቸውን በብቸኝነት የማሳደጉ ኃላፊነት ተደማምሮ ሌላ የሕይወት ፈተና ተጋረጠባቸው::

ባለታሪካችን ከሀዘናቸው ሳይወጡ ወደ ኖ”””ሩባት ባሕር ዳር ከተማ በመምጣት የነበራቸውን  ጥሪት  እየቆጠቡ ከልጆቻቸው ጋር መኖር ጀመሩ:: ኑሮ ፈተና ሆነባቸው፤ ልጆቻቸውን እንደበፊቱ ማብላት፣ ማልበስ… አቃታቸው::  ችግራቸውን የተረዱ ሰዎች “ልጆችሽ በጥሩ ሁኔታ እንዲያድጉ  ለአሳዳጊ ወደ ውጭ ላኪያቸው“ በማለት መከሯቸው:: እርሳቸው ግን  “ችግር ያልፋል:: ያን ጊዜ ደግሞ የሰውን ልጆች እያየሁ አላብድም!“ በማለት   የሚችሉትን ሁሉ ሠርተው ልጆቻቸውን ለማሳደግ እንደወሰኑ ያስታውሳሉ::

ሠርው የመለወጥ ጠንካራ  ዓላማ ያላቸው  ወ/ሮ ብዙሀረግ የቀራቸው ገንዘብ ሳያልቅ ቤት ተከራይተው በዶሮ ማርባት ሥራ ለመሰማራት ወሰኑ::  ልጆቻቸውን  ለማሳደግ በቁርጠኝነት የተነሱት  ወ/ሮ ብዙሀረግ አንድ ዶሮ በአንድ ብር አራት ሺህ የ45 ቀን  ጫጩቶችን ገዝተው  በተከራዩት ቤት  ማርባት ጀመሩ:: በወቅቱ የሥራቸውን  እንቅስቃሴ የተመለከተው ጥቃቅን እና አነስተኛ ጽ/ቤት በወቅቱ የመሥሪያ ቦታ ሰጣቸው::

መኖሪያቸውንም መሥሪያቸውንም እዛው በማድረግ ሥራውን በየቀኑ በልምድ በማዳበር የገቢ ምንጫቸው ሆነ::  እንዳሰቡት መቀጠል ግን አልቻለም፤ የዶሮ በሽታ ሲነሳ ሙሉ በሙሉ ሞቱ:: ወይዘሮዋ በገጠማቸው ኪሳራ ሳይደናገጡ  እንደገና ለመቀጠል መነሻ  ገንዘብ ለማግኘት ሌላ ሥራ ለመሥራት ወሰኑ::

በወቅቱ / 2004 ዓ.ም/ ቀበሌ 14 ያለው አረጋዊያን ሕንጻ ይሠራ ስለነበር በቀን ሥራ በ30 ብር ሂሳብ መሥራት ጀመሩ:: ሥራው ግን አቅማቸውን ፈተናቸው:: ሁኔታቸውን የተመለከቱ ሌሎች ሠራተኞች ከሸክሙ ይልቅ ግንባታው በሚከናወንበት አካባቢ ሻይ እና ቡና እንዲያቀርቡ ገፋፏቸው::

በሰዎች ግፊት መጀመሪያ ሻይ እና ቡና ቆየት ብለው ደግሞ   ቀለል ያለ  ምግብ ለተጠቃሚው ማቅረብ ጀመሩ፤ ገቢያቸውም ጥሩ ሆነላቸው::  አብዛኞቹ ደንበኞቻቸው በተለይ ደግሞ ሹፌሮች ምግባቸው  ጥሩ እንደሆነ በመረዳታቸው የተሻለ ገቢ የሚያገኙበትን ቦታ ጠቆሟቸው::  ጃዊ ካለው የስኳር ፋብሪካ ግንባታ  በሥራ ስለሚመላለሱ የምግብ አቅርቦት ፍላጎት ቢኖርም ጥሩ ምግብ አቅራቢ ስለሌለ ወደዛ እንዲሄዱ ምክር ለገሷቸው:: እርሳቸውም ሥራ ሳይመርጡ የተወሰነ ጥሪት ከቋጠሩ በኋላ ወደ ቀደመው የዶሮ ርባታ የመመለስ ሀሳቡ ስለነበራቸው ሀሳቡን ተቀብለው  የተወሰነ ጊዜ ከቆዩ በኋላ  ወደ ጃዊ ሄደው ለመሥራት ወሰኑ::

በወቅቱ ልጆቻቸው ትልቋ ሁለተኛ ክፍል፣ መካከለኛዋ ቅድመ መደበኛ/ኬጂ ሦስት/ እና መጨረሻው ኬጂ አንድ ተማሪ ነበሩ::  ልጆችን ለቤተሰብ እና ጓደኛ አደራ ሰጥተው በ150 ብር ተመላላሽ አብሳይ  በመቅጠር ወደ ጃዊ ከተማ ሄዱ::

ጃዊ በሚሠራው የስኳር ፋብሪካ አካባቢ ምግብ ቤት ከፈቱ:: ገበያቸው ከጠበቁት በላይ ሆነ::  ልጆቻቸውን እየተመላለሱ በማየት ለተከታታይ ሦስት ዓመታት በመሥራት 80 ሺህ ብር በመያዝ ወደ ባሕር ዳር ከተማ ተመለሱ::

በወቅቱ ልጆቹ በዕድሜ እያደጉ በመሆኑ ብዙ ጊዜን በአካል ተለይቶ መቆየቱ ለሌላ ችግር ያጋልጣቸዋል በሚል  ስጋት ከጎናቸው ሆነው  ለመሥራት ወሰኑ:: ልጆች  መሰረታዊ የሆነው ነገር ተሟልቶላቸው  እና ጥሩ በሚባል የግል ትምህርት ቤት እየተማሩ እንዲቀጥሉ ለማድረግ ደግሞ ያገኙትን ገንዘብ በባሕር ዳር ከተማ በሥራ በመሰማራት ገቢያቸውን ለማሳደግ ጊዜ አላባከኑም::

ወይዘሮዋ በፊት እንዳሰቡት በዶሮ ርባታ አልተሰማሩም:: ጥቃቅን እና አነስተኛ ዶሮ ለማርባት በሰጣቸው ቦታ ላይ ሁለት ጥጆችን በመግዛት በ2008 ዓ.ም በከብት ርባታ ተሰማሩ:: በወቅቱ እያንዳንዳቸው ዘጠኝ ሺህ ብር ያወጡ ሁለት የውጭ ዝርያ ያላቸውን ጊደሮች ገዙ:: ጥሩ ውጤት እንደሚኖራቸው በመተማመንም ነበር ወደ ሥራ የገቡት::

“የተወለድኩት ገጠር አካባቢ ስለሆነ ለእንስሳት ቅርበት አለኝ፤ ሥራውም ጥሩ ነው:: ነገር ግን ሥራውን ሥጀምር በልምድ  ያዳበርኩት ነገር ይበዛል” በማለት ሥራው ብዙም እንዳላስቸገራቸው ያስታውሳሉ::

በአሁን ወቅት የ17 ከብቶች ባለቤት ናቸው:: ከእነዚህ ውስጥ አሁን ላይ የወተት ምርት የሚሰጡ (የሚታለቡት) አራቱ ብቻ ናቸው:: ቀሪዎቹ ደግሞ ሦስቱ ወይፈን  ስለሆኑ ለሽያጭ እንደሚቀርቡና  ሌሎች  ደግሞ ክበድ (ለመውለድ የሚጠብቁ) መሆናቸውን በእጃቸው እየደባበሱ ነግረውናል::

ከብት ርባታ በፍቅር የሚሠሩት እንዲሁም ሙሉ ክትትልን እና ንጽህና የሚፈልግ ቢሆንም ለሠራ ደግሞ ለልፋት ተመጣጣን ዋጋ የሚከፍል እንደሆነ አስረድተዋል:: አሁን ከሚታለቡት ላሞች በቀን 40 ሊትር ወተት ለወተት ልማት እንደሚያስረክቡ ነግረውናል:: በሥራው ከራሳቸው አልፈው ለሁለት ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠር ችለዋል::

ያ ሁሉ ችግር፣ ያ ሁሉ ውጣ ውረድ አልፎ በጥረታቸው ባፈሩት ሀብት ከልጆቻቸው በተጨማሪ የዘመድ ልጅም አብራ ማሳደግ  እንደቻሉ ወ/ሮ ብዙሀረግ ነግረውናል:: አሁን ላይ የመጀመሪያ ልጃቸው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በዲግሪ ተመርቃለች::  ሁለተኛዋ ደግሞ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በክሊኒካል ፋርማሲ ቀጣይ ዓመት ተመራቂ ናት፣ ሦስተኛው ደግሞ ቪዲዮግራፊ  በመሠልጠን አሁን አዲስ አበባ ከተማ በሥራ ላይ ይገኛል::

በቪድዮግራፊ ሥራ ላይ የሚገኘው ልጃቸው እዮብ በላቸው እናቱ እነሱን ለማሳደግ ተነግሮ የማያልቅ ችግሮችን እንዳሳለፉ ያስታውሳል::  አሁንም ድረስ ልጆቻቸው መሥመራቸውን እንዳይስቱ በማስተካከል እና በመደገፍ ትልቅ አስተዋፅኦ እያደረጉ ያሉ ጀግና እናት እንደሆኑ ነው የሚገልፀው::

በቀጣይ በማድለቢያቸው ትልቁን የመብራት ቆጣሪ  በማስገባት ከብቶችን ከማርባት በተጨማሪ የከብት መኖ ማቀነባበሪያ ለመክፈት ሃሳብ አላቸው:: ልጆቻቸውም  ቢሆን ትምህርታቸውን በአግባቡ ካጠናቀቁ በኋላ የእርሳቸውን ሙያ በአግባቡ እንዲመሩ ፍላጎት እንዳላቸው ነው የገለፀልን::

ሥራውን በጀመሩ በ10 ዓመት ውስጥ ኑሮን በአግባቡ ከመምራት በተጨማሪ ተደራጅተው የመኖሪያ ቤት ቦታ የማግኘት ዕድል አግኝተዋል:: ሙያቸውንም ወደ ቀጣይ ትውልድ የማስተላለፍ እቅድ ለማሳካት በበለጠ እንደሚሠሩ ጠቁመዋል::

እናት እና አባቷን  ከ10 ዓመት በፊት ያጣችው ወ/ሮ ሙሉእመቤት ይልማ ወ/ሮ ብዙሀረግ   ከሦስት ልጆቻቸው በተጨማሪ አራተኛ ልጅ ሆና በጥሩ እንክብካቤ ማደጓን ትመሰክራለች::  ወ/ሮ ሙሉእመቤት ትምህርቷን ከመከታተል በተጨማሪ የሽመና ሙያ በመሰልጠን ወደ ሥራ ገብታለች:: አሁን ላይ  ትዳር መስርታ ልጅ አፍርታለች:: ይህ ሁሉ የሆነው ደግሞ በአክስቷ ድጋፍ እንደሆነ ገልጻለች:: ከአክስቷ ሥራን ሳይንቁ ትንሽ ትልቅ ሳይሉ መሥራት እንደሚቻል መገንዘብ መቻሏንም ነው የምትገልፀው::

(ማራኪ ሰውነት)

በኲር የሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here