የአማራ ክልል ጤና ቢሮ እና ኤም ኤስ አይ ኢትዮጵያ (ማሪስቶፕስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ – MSI Ethiopia) መካከል የ291 ሚሊዮን ብር በላይ የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራርመዋል::
ፕሮጀክቱ በእናቶችና ወጣቶች ጤና እና ሥነ ተዋልዶ ዙሪያ እና ሥርዓተ ምግብ አገልግሎትን ለማሻሻል የሚያስችል ነው:: ስምምነቱም የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አብዱል ከሪም መንግሥቱ እና የኤም ኤስ አይ ኢትዮጵያ ካንትሪ ዳይሬክተር አበበ ሽብሩ(ዶ/ር) መካከል ተፈርሟል::
ለአራት ዓመታት የሚቆየው ይህ የፕሮጀክት ስምምነት በክልሉ በሚገኙ 15 ዞኖች እና 41 ወረዳዎች በሚገኙ 60 ጤና ጣቢያዎች ይተገበራል:: ለዚህም 291 ሚሊዮን 464 ሺህ በላይ በጀት እንደሚሰጥ እንደሚደረግ የኤም ኤስ አይ ኢትዮጵያ ካንትሪ ዳይሬክተር አስታውቀዋል::
በኤም ኤስ አይ ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም በአማራ ክልል በሥነ ተዋልዶ ጤና ዙሪያ እናቶችንና ወጣቶችን መሠረት ያደረገ በርካታ ሥራዎችን ማከናወኑን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል:: በዚህ የፕሮጀክት ስምምነት ላይም ድርጅቱ ከ130 እስከ 150 አካባቢ ለሚደርሱ በባሕር ዳር፣ በደብረ ማርቆስ እና በደሴ ለሚገኙ የጤና መድን ተጠቃሚዎች የ500 ሺህ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል::
የአማራክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አብዱል ከሪም መንግሥቱ በበኩላቸው ኤም ኤስ አይ ኢትዮጵያ በአማራ ክልል በጤናው ዘርፍ ለሚያከናውናቸው በጎ ተግባራት ምስጋና አቅርበዋል::
(ሳባ ሙሉጌታ)
በኲር የካቲት 17 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም