“ዓባይ ጉደል ብለው አለኝ በታህሣሥ
የማን ሆድ ይችላል እስከዚያው ድረስ”
ለተረት የታደለ፤ ለአፍ የጣፈጠ ወንዝ እንደ ዓባይ የለም:: አንዳንድ ሰው ምንም ዓይነት ተረትና ምሳሌ ባይችል ቢያንስ “አባይ ማደሪያ የለው ግንድ ይዞ ይዞራል” የሚለው ተረትና ምሳሌ ከአፉ አይታጣም:: እርግጥ ነው፤ አባይ መንገደኛ ነው፤ብዙ ርቆ ይሄዳል:: በእርግጥም የግዝፈቱንና የገናናነቱ እና ያህል ጥቅም ላይ አልዋለም ::
ክረምት አልፎ የዓባይ ውሃ ሙላት ጎድሎ ታህሣሥ ድረስ መታገስ አቅቶት የናፍቆት ግጥም እና እንጉርጉሮ ለመግጠም የታተረ፣ እስከዚያ መታገስ ያቃተው ትውልድ ዓባይን ጥቅም ላይ ለማዋል ለምን ገደደው? ነው ጥያቄው::
አንዳንድ አባባሎች ለስንፍና፣ ለሰበብ በር ይከፍታሉ:: እነዚህን አባባሎች ላለመቻል እንደሰበብ ወስደን ላልተሳካልን ነገር እንደ ምክንያት በመቁጠር ራስን ለማሳመን እንጠቀምባቸዋለን::
ዓባይን ላለመጠቀማችን ተረቱን እንደ ምክንያት፤ ምሳሌያዊ ንግግሩን እንደአይነኬ በማየት ዓባይ መንገደኛ እንዲሆን እድል ሰጥተነው ኖረናል::
ከዚህ ሁሉ ተረት ውጭ ሁሉም የማይናገረው እና በውስጡ የያዘው ቁጭት እንዳለ ማሳያው ግን የሕዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ መጣል ነው::
የሕዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ ብስራት ለዘመናት በተረት ሸንግለን እንዲጓዝ እድል የሰጠነው እና መንገድ የከፈትንለትዓባይ ከልባችን እንዳልነበረ በዚሁም በሁሉም ሰው ልብ ውስጥ ቁጭት እንደነበረ ማሳያ ነው::
አቅሙ የፈቀደ ሁሉ ያለውን ሳይሰስት እየሰጠ እዚህ ደርሷል:: በዚህ ግድብ ግንባታ ሂደት መላ ኢትዮጵያውያን እውቀታቸውን፣ ጉልበታቸውን እና ገንዛባቸውን አስተባብረው በጋራ ለመቆ እንዲሁም በጋራ ለመስራት እንደምክንያት የሆነ ብሎም ግድቡ የሁሉም መሆኑን ያሳየ ተግባር ፈጽመዋል::
ግንባታው ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ሕዝቡ ከ23 ቢሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አድርጓል:: ይህን ያህል ገንዘብ መሰብሰብ የተቻለው ደግሞ ከቦንድ ሽያጭ እና ስጦታ፣ በ8100 አጭር የጽሑፍ መልዕክት እና ከኢትዮጵያ ነጻ አካውንት እንዲሁም ከውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን /ከዳያስፖራዎች/ ነው::
የሕዳሴ ግድብ ተጠናቆ በመጭው መስከረም በድምቀት ለማስመረቅ ዝግጅት እየተደረገ ነው:: የሕዳሴ ግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ወደ ልማት ሲሸጋገርም የተፋሰሱን ሀገራት ተጎጂ የሚያደርግ ሳይሆን ለቀጣናዊ የጋራ ልማት በረከት በጋራ ለመልማት የሚያስችል እና የሁሉንም ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ ነው:: ለእኛ ለኢትዮጵያውያን በአንድ የመቆምና በጋራ የመፈጸም ማሳያና የቁጭታችንም መገለጫ ነው::
በኲር የሐምሌ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም