የመጪው ዘመን ተስፋ

0
158

ሽምብራ የተለያዩ ዝርያዎች ያሉት  ድርቅን ተቋቋሚ፣ ተመርቶ ለምግብነት ሲውልም የኘሮቲን ይዘቱ ከፍተኛ፣ ለመጪው ዘመን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ተስፋ የሚጣልበት መሆኑን ሳይንስ ዴይሊ ድረ ገጽ ለንባብ አብቅቶታል::

በኦስትሪያ ቪዬና ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የተመራው ዓለም አቀፍ ቡድን ባደረገው ጥናት ሽምብራ የተለያዩ ዝርያዎች ያሉት ከመሆኑ ባሻገር በከተሞች አካባቢም ቢሆን ሊመረት የሚችል፣ ድርቅን ተቋቋሚ ሰብል መሆኑን አረጋግጧል::

በአብዛኛዎቹ ሃገራት ረዘም ላለ ጊዜ በተከሰተው የዓየር  ንብረት ለውጥ መንስኤነት የሰብል ልማት ተስተጓጉሏል፤ ምርታማነት ቀንሷል፤ የምግብ ዋስትና መረጋገጥም ስጋት ላይ ወድቋል::  እስከ አሁን የተለያዩ ዝርያ /genetic diversity/ ባላቸው ላይ ከመመርኮዝ ይልቅ በውስን ዓይነቶች ላይ ብቻ ትኩረት ተሰጥቶ መመረቱ የምግብ ዋስትና ላለመረጋገጡ ተጠቃሽ ምክንያት ሆኗል:: ለአብነትም ሰባት ሺህ ከሚደርሱ ለምግብነት ከሚውሉት ምርቶች ውስጥ በዘጠኝ ምርቶች ላይ ብቻ ነው የምግብ ፍላጐቱን ለማሟላት መሰረት ያደረገው::

ተመራማሪዎቹ የአዝርእት የዘር ዓይነት መጥበብ ወይም የተለያዩ ዓይነቶችን መሰረት አድርጐ አለማምረት ከጠቀሜታው የበለጠ ጐጂነቱ እንደሚያመዝን አስታውቀዋል:: ምክንያታቸው ደግሞ ለበሽታ፣  ለተባይ እና ለድርቅ አጋልጦ ምርታማነትን የሚቀንስ መሆኑን ነው ያሰመሩበት::

ዓለም አቀፍ የምርምር ቡድኑ የተለያዩ የሙከራ ተግባራትን፣ ሁለገብ ጥናትና ክትትልን በሽምብራ ላይ አካሂዷል:: በውጤቱም ሽምብራ ለመጪው ዘመን ተስፋ የሚጣልበት አዝርእት ሆኖ ነው የተገኘው:: ለመጪው ዘመን የግብርናው ዘርፍ ዘላቂነት የተለያዩ የዘረመል ልዩነት ያላቸው አዝርእትን ጠብቆ ማቆየት ወሳኝ መሆኑን ነው  ተመራማሪዎቹ ያስገነዘቡት።

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር ጥቅምት 18  ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here