የበዓል ሰሞን እና ጤናማ የአመጋገብ

0
300

ሥርዓተ ምግብ ማለት የተመገብነው ምግብ በሥነ ሕይወታዊ ሂደቶች በማለፍ በአጠቃላይ በሰውነት ግንባታ ዙሪያ እድገት ማምጣት ነው:: ዋና  ዋና ምግቦች የሚባሉት በብዛት ኀይል የሚሰጡ እና የተመገብነው ምግብ በሰውነታችን ውስጥ ሥርዓተ ኡደቱን ጠብቆ በትክክል እንዲሠራ የሚረዳ መሆኑን በአማራ ክልል ጤና ቢሮ የሥርዓተ ምግብ ኦፊሰር አቶ ባይለየኝ ቢምረው ተናግረዋል::

ንዑስ ንጥረ ምግቦች የሚባሉት ደግሞ ስርዓተ ዑደቱ እንዲካሄድ ወሳኝ ሚና የሚጫወቱ ሲሆን ሁለቱም ዓይነት ንጥረ ምግቦች ከአካባቢያችን በቅርብ የሚገኙ ናቸው::

በአጠቃላይ ጤናማ አመጋገብ የሚባለው ሰውነትን የሚገነቡ  የፕሮቲን  ይዘት ያላቸው  ከእንስሳት  እና ከጥራጥሬ  የሚካተቱት ስጋ፣ ዶሮ ፣ እንቁላል፣ የእናት ጡት ወተት፣ ባቄላ፣ ለውዝ፣ ምስር፣ ሽንብራ፣  አሳ፣ አይብ እና ወተት መመገብ ሲቻል ነው:: ዳቦ፣ ጤፍ፣ በቆሎ፣ ቆጮ ፣ ድንች ፣ ስኳር አገዳ፤ ማር፤ ጣፋጭ ፍራፍሬዎች፣ ፓስታ፣ ማኮሮኒ እና ሽሮ ደግሞ ኀይል እና ሙቀት ሰጭ ምግቦች ውስጥ የሚካተቱት ናቸው::

ኦፊሰሩ እንደሚገልፁት ለሰውነት ጠቃሚ  ምግቦችን አመጣጥኖ መውሰድ ጤናማ ቢያደርግም እንደ ሀገር ያለው የአመጋገብ  ሥትዓት ግን ጤናማ የሚባል አደለም::

እንደ አቶ ቢምረው ማብራሪያ በልማድ ዘወትር በገበታችን የሚቀርብ ምግብ የተሰባጠረ ሳይሆን  አንድ ዓይነት ነው::  በአሁን ወቅት ደግሞ በየሱቆች  የሚገኙ በፋብሪካ የሚመረቱ የታሸጉ ምግቦች እና መጠጦች ናቸው:: እነዚህ የምርት ውጤቶች በተለይ ለሕፃናት እና ህሙማና  ጭምር መሰጠቱ ደግሞ ሌላ የጤና ጉዳት እያስከተለ ነው:: ከዚህ መረዳት የሚቻለውም ሥለጤናማ አመጋገብ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለመፍጠር ብዙ እንዳልተሠራ ነው::

የቫይታሚን እጥረትን ለመከላከል  ጎመን  እና ቆስጣ፣ ከፍራፍሬ ማንጎ ፣ብርቱካን እና  ፓፓዬ  መመገብ እንደሚገባም ኦፊሰሩ ጠቁመዋል::  በሽታን ለመከላከል ደግሞ አትክልት እና ፍራፍሬዎችን  አሰባጥሮ መመገብ  ሲቻል ነው:: ጮማ፣ ጨው እና ስኳር ዕድሜ እየጨመረ ሲሄድ ከገበታ እንዲርቁ አልያም ቅባት ያለው ምግብን እንዲቀንሱ  ይመከራል::

የሥርዓተ ምግብ ኦፊሰሩ ጤናማ የሆነ የፆም ወቅት አመጋገብን በተመለከተም ሲያብራሩ የኦርቶዶክስ ሃይማኖት እምነት ተከታዮች ከቅባት ርቀው እና ቀኑን ሙሉ ፆም ውለው ቀለል ያሉ ምግቦችን ሽሮ፣ አትክልት… ሲመገብ ነው የሚቆዩት:: ችግር የሚሆነው ታዲያ በፆም የቆየው አመጋገብ በዓል ሲመጣ ቀጥታ ወደ ቅባታማ ምግቦች ይገባል:: በዚህ ወቅት ጨጓራ ደግሞ ከቆየበት ልምድ አንፃር ቀስ በቀስ ስለሚሠራ ለመፍጨት ይቸገራል::

ጨጓራ ወደ ነበረበት ለመመለስ ደግሞ ጊዜ ይፈልጋል:: በዓል ሲመጣ ምግቡ ሁሉ ቅባት የበዛው ሚጠጣው ደግሞ በብዛት አልኮል ስለሚሆን ለጤና ችግር ያጋልጣል:: በዚህ ጊዜ  ለረጅም ጊዜ ከቅባት ርቆ የቆየ ጨጓራ ለህመም የመዳረግ አጋጣሚው  ከፍተኛ ይሆናል:: ይህ ሲሆን ጥንቃቄ የጎደለው አመጋገብ ይከሰታል:: ይህን ተከትሎም  ሆድ መንፋት፣ ሆድ ቁርጠት፣ ጨጓራ ማቃጠል እና ሌሎችንም ህመሞች ሊያስከትል እንደሚችል ባለሙያው ገልፀዋል::

ከፍተኛ ስብ ያለባቸው ምግቦች የካሎሪ ክምችታቸው ከፍተኛ ስለሚሆን በተደጋጋሚ ከተመገብናቸው ያልተፈለገ የስብ ክምችት/ /ኮሌስትሮል/ እንዲጨምር ያደርጋል:: ይህም የልብ ህመም እና ለሰውነት መዛል/ስትሮክ/ ተጋላጭነትን ይጨምራል። ከመጠን ያለፈ ውፍረት እና ስኳር በሽታም ያስከትላል።

በባእላት ወቅት የሚዘወተሩት ጥሬ ሥጋ እና ሌሎች ያልበሰሉ ምግቦች ደግሞ  እንደ ኮሶ በሽታ ዓይነት ያስከትላሉ::  በተለይ ሥጋው የሚታረድበት አካባቢ በጤና የተረጋገጠ ካልሆነ ለበሽታ ያጋልጣልና ህብረተሰቡ የእርድ ከብቶችን ጤንነት በማረጋገጥ በቄራዎች ሕጋዊ በሆነ መንገድ እንዲያሳርድ አሳስበዋል:: በመሆኑም በዓላትን የጤና መታወክ ሳያጋጥም ለማሳለፍ  የሚዘጋጀው ምግብ በአግባቡ ንጽህናው  የተጠበቀ መሆን እንዳለበት ኦፊሰሩ መክረዋል::

በበዓል ወቅት  በተለይ የመጀመሪያዎቹ ቀናት በአንድ ጊዜ ብዙ ከመመገብ መቆጠብ እንደሚገባ አቶ ቢምረው መክረዋል:: ለአብነት ዶሮ ከበላን ዶሮ በተፈጥሮ  ቅባት አለው:: ከዚህ በተጨማሪ  ቅቤ ፣ እንቁላል ፣ ወተት ፣እርጎ ፣ጥሬ ሥጋ… በአንድ ጊዜ ባይወሰድ ለጤና ጥሩ ነው::  የግድ ከወሰዱም ደግሞ መጠናቸው በጣም ጥቂት  መሆን እንደ ሚገባው ነው ባለሙያው የሚመክሩት ::

በአጠቃላይ በእለት ከእለት ምግብ አጠቃቀም ሁለንም ንጥረ ነገር ያቀናጀ ካልሆነ አንዱን አዘውትሮ የመመገብ ልምድ በጤና ላይ ችግር እንደሚያስከትል አምኖ ምግቦችን በየአይነቱ አሰባጥሮ መመገብ እንደሚገባም ነው ባለሙያው ያሳሰቡት::

ጤናማ የአመጋገብ ሥርአት የሚባለው የአትክልት እና ፍራፍሬ ስብጥር ሲኖር ነው::  ነገር ግን ከፀረ ተባይ መድኃኒቶች ጋር ተያይዞ  በተለይ ጎመን ፣ ቆስጣ፣ ቲማቲም  የመሰሉ አትክልት እና ፍራፍሬዎችን ከገበታ የማራቅ ሁኔታ ይስተዋላል፤ ለዚህ መፍትሄው ምንድነው? ስንል ለኦፊሰሩ ጥያቄ አነሳን:: እንደ ሀገር አቀፍ ችግሩ ተነስቶ በተለያየ መድረክ ከግብርና ቢሮ ጋርም እየተነጋገሩ እንደሆነ አቶ ቢምረው ጠቁመዋል:: ይሁን እንጅ ወደ ፊት ይሻላል ተብሎ ቢጠበቅም በአሁኑ ወቅት ገና መፍትሄ  ያልተቀመጠለት ነገር እንደሆነ ተናግረዋል::

የምግብ አለመመጣጠ  ከፍተኛ የጤና ችግር ያስከትላል:: በተለመደው የአመጋገብ ሥርዓት ብቻ የመሄድ ነገር በመኖሩ ይህንን ለመቀየር በቀን ውስጥ ከአትክልትም ፣ከፍራፍሬም ፣ከጥራጥሬም እያሰባጠሩ የመመገብን ልምድ ሁሉም በየቤቱ ሊተገብር እንደሚገባው አሳስበዋል::

(ማራኪ ሰውነት)

በኲር ሚያዝያ 28 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here