የብዝኃ ሕይወት ውድመት እንዳይከተል

0
136

በዓየር ንብረት ቀውስ የሚደርሰውን ተፅእኖ መቀነስ ወደሚያስችል ከብክለት የፀዳ የኃይል አማራጭ ለመሸጋገር የሚደረግ የማእድን ቁፋሮ የብዝሃ – ሕይወት ውድመትን ሳያስከትል ሊሠራ እንደሚገባ ቴክኖሎጂ ዶት ኦርግ ድረ ገጽ ለንባብ አብቅቶታል::

በእንግሊዝ የካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ በመረጃ ምንጭነት ለንባብ እንዳበቃው ከብክለት ወደ ፀዳ የኃይል ምንጭ መሸጋገር ግድ መሆኑ ታምኖበታል:: ሆኖም ሽግግሩን እውን ለማድረግ  መሥሪያ የሆኑት መሰረታዊ ቁሶች ሊቲዬም እና ኮባልትን የመሣሰሉ ማዕድናትን ለማውጣት የሚደረገው ቁፋሮ በቀጣናው የሚገኝ ብዝሃ ሕይወት ላይ ውድመት እንደሚያደርስ ተመራማሪዎቹ አስታውቀዋል::

በአዲስ መልኩ በተካሄደ ጥናት እና ምርምር ከአራት ሺህ የሚበልጡ አከርካሪ ያላቸው የዓእዋፍ እና የዓሣ ዝርያዎች የመጥፋት ስጋት እንዳዣበበባቸው ማረጋገጣቸውን አስታውቀዋል- ተመራማሪዎቹ:: በተጨማሪም ስጋቱ በማዕድን ማውጫው ቦታ ብቻ የተገደበ አለመሆኑን ያብራሩት ተመራማሪዎቹ ርቀው የሚኖሩ ዝርያዎችም የጉዳቱ  ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉ ነው የጠቆሙት:: ለዚህ ደግሞ በተበከሉ የውኃ መፋሰሻዎች፣ በሚሠሩ አዳዲስ መዳረሻ የመንገድ መሰረተ ልማቶች የደን መጨፍጨፍ አይቀሬ መሆኑን ነው በትኩረት ያነሱት::

ከማእድን ማውጣት ጋር ተያይዞ የሚደርሰውን የብዝሃ – ሕይወት ውድመት ለመቀነስ መንግሥታት እና የማእድን ኢንዱስትሪው በቅንጅት ተናበው መሥራት እንደሚገባቸውም ነው የጠቆሙት – ተመራማሪዎቹ::

በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ መሪ ተመራማሪው ኘሮፌሰር ዴቪድ  ኤድዋርድ በዓየር ንብረት ብክለት የሚደርሰውን ተፅእኖ ለመቀነስ ከብክለት የፀዳ ኃይል ማምረት አማራጭ የሌለው መሆኑን አስምረውበታል::

ይህንኑ እውን ለማድረግም የማእድን ፍለጋው በርካታ ብዝኃ ሕይወት በሚገኝባቸው  አካባቢዎች ጉዳት ያደርሳል:: ሆኖም የጉዳቱን ደረጃ መቀነስ ወይም ማመናመን ተገቢና ግድ መሆኑን ነው በአፅንኦት ያሳሰቡት::

ተመራማሪው እንዳመላከቱት በማዕድን ቁፋሮ ምክንያት  ዓሣዎች፣ ተሳቢ እንስሳት፣ አእዋፍ ከሁሉም በላይ  በአነስተኛ ክልል ብቻ የሚገኙ ዝርያዎች በከፍተኛ ደረጃ ለአደጋ የተጋለጡ ናቸው::  ለዚህም ወደ ሌላ አካባቢ ፈልሰው መኖር አለመቻላቸውን ነው በምክንያትነት የጠቀሱት::

ሌላው በአብነት ከተጠቀሱ እውነታዎች ማዕድን ለማውጣት የሚደረግ ቁፋሮ ከወንዞች ወይም ከውኃ መስመሮች ጋር ተገናኝቶ ረዢም ርቀት ተጉዞ ሰፊ ስነ ምህዳር ሊበክል መቻሉ  ከፍተኛ ስጋት መሆኑ ነው በማደማደሚያነት ያስፈሩት – ተመራማሪዎቹ::

 

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር ነሐሴ 6 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here