የእናቶችን እና ህጻናትን ጤና ለመጠበቅ በትኩረት ይሠራል

0
120

የጤናማ እናትነትን ወር በማስመልከት የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ከሰሞኑ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ የእናቶች እና ሕጻናት እንዲሁም የጨቅላ ሕጻናትን ጤና ማስጠበቅ የመንግሥት ትኩረት ነው ብለዋል::

እናቶች ከወሊድ ጋር ተያይዞ ተገቢውን የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ የጤና ተቋማትን እና አስፈላጊ የሕክምና ግብዓቶችን ተደራሽ የማድረግና የሕክምና ባለሙያዎችን አቅም የማሳደግ ሥራ እየተሠራ ነው ብለዋል።

የእናቶችን ሞት ለመቀነስ እና ቅድመ ጥንቃቄዎችን ለማድረግ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር እየተሠራ ነው ያሉት ሚኒስትሯ በወሊድ ምክንያት የሚሞቱ እናቶችን ቁጥር ለመቀነስ ጤና ኬላዎችን እና ጤና ጣቢያዎችን የማስፋፋት ሥራ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል።

ሚኒስትሯ በመግለጫቸው እንዳሉት ለእናቶች ሞት ምክንያት ከሆኑት በሽታዎች መካከል የማህጸን በር ካንሰር አንዱ ነው። በመሆኑም እንደ ሀገር የማህጸን በር ካንሰርን ለመከላከል ከጤናማ እናትነት ወር ጋር በማያያዝ በሽታውን ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት ይከናወናሉ።

ዶክተር መቅደስ እንዳሉት የጤናማ እናትነት ወርን ምክንያት በማድረግ ጥራቱን የጠበቀ የወሊድ አገልግሎት ለእናቶች ለመስጠት አቅም በሚፈጥሩ መርኃ ግብሮች ወሩ የሚከበር ይሆናል::

የጤናማ እናትነት በየዓመቱ በጥር ወር ሙሉውን ቀናት የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ይከበራል።

(ሳባ ሙሉጌታ)

በኲር የጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here