የዝዋይ ኃይቅ ከአዲስ አበባ 162 ኪሎ ሜትር፣ ከአዳማ ከተማ ደግሞ 107 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል:: ኃይቁ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ክልል ዋና ከተማ አዋሳ ሰሜናዊ አቅጣጫ 113 ኪሎ ሜትር ርቆ ከሚገኘው ከፍታ ተንጣሎ ይታያል::
የዝዋይ ኃይቅ በምስራቅ አፍሪካ የስምጥ ሸለቆ ቀጣና የተካተተ ሲሆን ከፍታው ከመሬት ወለል በላይ 1636 ሜትር ተለክቷል::
የኃይቁ አጠቃላይ ስፋት 434 ኪሎ ሜትር ካሬ ተለክቷል:: የባህር ዳርቻው ርዝመት 137 ኪሎ ሜትር ሲሆን ዙሪያው በ7300 ካሬ ኪሎ ሜትር ተፋሰስ ውስጥ የተከበበ ነው::
ኃይቁ ሁለት መጋቢ ወንዞች አሉት- በደቡብ ምስራቅ የካታር ከሰሜን ምእራብ አቅጣጫ መቂ ወንዝ ናቸው:: ከኃይቁ የሚወጣ ብቸኛው የቡልቡላ ወንዝ ብቻ ነው::
በሐይቁ ዳረቻ በርካታ የዓሳ ጥበስ መሸጫ ቤቶች ይገኛሉ:: በኃይቁ መካከል አምስት ማለትም ቱሉጉዶ፣ ፀደቻ፣ ገሊላ፣ ፉንዱሮ እና ደብረ ሲና የተሰኙ ደሴቶች ይገኛሉ:: በእያንዳንዳቸው ላይ የኦሮቶዶክስ ሀይማኖት ገዳማት ተተክሎባቸዋል:: ከደብረሲና በቀር በሁሉም ደሴቶች ከ14ኛው እስከ 17 ኛው ክፍለ ዘመን ባለው የሰፈሩ የ “ዛዬ” ብሄረሰብ መኖሪያ ናቸው::
ከአእዋፍ “ፔሊካን” የተሰኙት ግዙፍ ባለምንቃር፣ ከዓሳ ዝርያም ቀሮሶ እና ነጭ ዓሳ በብዛት ይገኛሉ:: በኃይቁ ላይ ያሉ ደሴቶችም በተለያዩ የእፅዋት ዓይነቶች የተሸፈኑ ናቸው::
የዝዋይ ኃይቅ እና በላዩ ላይ የሚገኙ ደሴቶች ኃይማኖታዊ በዓላት እና ነባር ዝርያዎች በ2018 እ.አ.አ በተባበሩት መንግስታት የአካባቢ፣ የሳይንስ እና ባህል ድረጅት ተመዝግቦ እውቅና አግኝቷል::
ለዘገባችን በመረጃ መንጭነት ስኘሪንግስ አርሲሲ ዶት ኦርግ፣ ሳፈሪ ቡኪንግስ እና ብሪሊያንት ኢትዮጵያ ድረ ገፆችን ተጠቅመናል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የግንቦት 4 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም