በካናዳ ኩቤክ ትሮይስ- ራቪዬሪስ በተሰኘ ቀጣና የጋራ መኖሪያ ህንፃ ባለንብረት ግለሰብ ባጋጣሚ ጐራ ባሉበት አንዱን በሩን ሲከፍቱ ግድግዳ እና ጣሪያው፣ የቤት እቃዎቹ ጭምር በግግር በረዶ ተሸፍነው ማግኘታቸውን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ አስነብቧል::
ባለንብረቱ ዣክ ናውልት ከጋራ መኖሪያ ቤቶቹ የአንዱን በር ሲከፍቱ በበረዶ የተሰራ የቤተመንግሥት ፍርስራሽ የተመለከቱ እንደመሰላቸው ነው የተናገሩት:: ግድግዳው፣ ወለሉ፣ ጣሪያው፣ በየጥጋ ጥጉ የተቀመጡ ቁሳቁስ ሳይቀሩ ረቂቅ ቅርፃ ቅርፅ መሰለዋል – በግግር በረዶ::
ባለንብረቱም የሁነቱን መንስኤ ተዟዙረው ለመመልከት ሞክረዋል:: በፍተሻቸው ተከራዩ ግለሰብ ለቀናት ከቤት ለእረፍት ሲሄዱ የኤሌክትሪክ ፍጆታቸውን ለመቆጠብ በማሰብ ማሞቂያውን ማጥፋታቸው ወይም ኃይል መቋረጡ መንስሄ መሆኑን አረጋግጠዋል::
ተከራዩ የማሞቂያ ክፍያውን ለመቆጠብ ኃይል በማቋረጣቸው የውኃ ማስተላለፊያ ቱቦዎች ፈንድተው ግድግዳዎች ሻግተው ለከፍተኛ ወጪ ዳርጓቸዋል:: በዚህም አከራዩ ተከራዩን ተጠያቂ እንደሚያደርጉ ነው የተጠቆመው- በድረ ገጹ::
ዣክናውልት ሁሉም ነገር ውድ መሆኑን እና ወጪ መጨመሩን ጠቁመው ተከራዩ ወጪ ለመቀነስ የፈፀሙት ስህተት የበለጠ ወጪ ማስከተሉን ነው ያሰመሩበት::
አከራዩ ባጠቃላይ የተከሰተውን ጥፋት ወይም በመኖሪያ ቤቱ እና ቁሳቁስ ላይ የደረሰው ጉዳት በአስር ሺህ ዶላሮች እንደሚገመትም ነው ያሰመሩበት::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የጥር 25 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም


