ከባድ ዝናብ እና ደረቅ ከባቢ ዓየር መፈራረቁን ተከትሎ፣ የዓየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ሙቀትን በማስፈኑ የሰደድ እሳት በሁለት እጥፍ መጨመሩን ሳይንስ ዴይሊ ድረ ገጽ ከሰሞኑ አስነብቧል::
በ2022 እስከ 2023 እ.አ.አ በአሜሪካ ካሊፎርኒያ የክረምት ወቅት የጣለው ዝናብ አይሎ በጐርፍ መጥለቅለቅ እና በበረዶ ከተሞች ተቀብረው ታይተዋል:: በየሸለቆዎች የበረዶ ናዳ እንዲሁም የመሬት መንሸራተት እየተስተዋለ እንደነበር የካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች አስታውቀዋል::
የዓየር ንብረት ተመራማሪዎች ቡድን ከ20ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ አስከፊው የዓየር ንብረት ጅራፍ ወይም ግርፋት ከ31 በመቶ ወደ 66 በመቶ ማደጉን አረጋግጧል::
የተመራማሪዎች ቡድኑ ዓለም በፓሪስ የዓየር ንብረት ስምምነት ካስቀመጠው የአንድ ነጥብ አምስት አማካይ ገደብ ለማለፍ ተዘጋጅታለች ሲሉም መጪውን ዳፋ በባለሙያዎች የተደረጉ ጥናታዊ ትንታኔዎች ጋር በማጣቀስ ስጋታቸውን አስፍረዋል::
የጐርፍ እና የድርቅ አደጋ ተባብሶ ከከባቢ ዓየር፣ ከዕፅዋት እና ከአፈር ውስጥ ርጥበትን እየመጠጠ ነው፤ ይህም ከዝናብ እጥረት ባለፈ ድርቅን አባብሷል ባይናቸው የባለሙያዎቹ ቡድን::
በመሆኑም ይላሉ አጥኚዎቹ ለዓለማችን በሙቀት መጨመር ከከባቢ ዓየር ምን ያህል ርጥበት እንደሚመጠጥ ማረጋገጫ፣ ማሳያ ነው:: የተመራማሪዎቹ ቡድን መሪ ዳንኤል ስዋይን የከፋውን ወይም ኃይለኛ ዝናብን ወይም የከፋ ድርቅን በተናጠል ማየት፣ ማጥናት፣ መከታተል እንደማይቻል ነው ያሰመሩበት:: ለዚህ ምክንያቱ የዝናብ መጠኑ መጨመሩም ሆነ በየመካከሉ የሚከተለውን ድርቅ አመጣጥኖ እና አቀናጅቶ መፍትሄ መሻት ግድ መሆኑን ነው በማጠቃለያነት ያሰመሩበት::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የጥር 12 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም