የወፍ ዋሻ ደን በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን የሚገኝ ተፈጥሯዊ ደን ነው:: ስፋቱም 6000 ሄክታር ተለክቷል:: ደኑ ከአዲስ አበባ በስተሰሜን 130 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በጣርማ በር፣ ባሶና ወራና እና አንኮበር ወረዳዎች ነው የተከለለው::
ተፈጥሯዊው ጥብቅ ደኑ ከ2000 እስከ 3700 ሜትር ከፍታ ባለው መልካምድር ነው የሚገኘው፤ ከእፅዋት 25 ዝርያዎችን ይዟል:: በአቀማመጡ ከፍታ ባላቸው ቦታዎች የጓሣ ሣር፣ እና ጦስኝ፣ ጅብራ ከዚያ አነስ ባለው ዘመናትን ያስቆጠሩ የፅድ እና የወይራ ዛፎችም መገኛ ነው::
ከዱር እንስሳት ጭላዳ ዝንጀሮ፣ ተኩላ፣ ጅብ፣ አነር መኖራቸው ተረጋግጧል:: ከዓእዋፍ የ158 ዝርያዎች መገኛ ነው፤ ከነዚህ ውስጥ የአንኮበር ሶረኔ፣ ላሜርገየር ቅልጥም ሰባሪ እና “አቢሲኒያን ካት በርድ”ን ይዟል::
በደኑ ቀጣና በእግር ተዟዙረው ለሚጐበኙ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች የሚደገፉ በአካባቢው ማህበረሰብ አቀፍ የእንግዳ መቀበያ ተዘጋጅተው አገልግሎት ይሰጣሉ:: የጋራ መፀዳጃ ቤት፣ መታጠቢያ እና ባህላዊ ምግብ፣ አረቄ እና ቡናም በማስተናገጃዎቹ ይገኛሉ::
የወፍ ዋሻ ደን በተፈጥሮ የተቸረ የብርቅዬ እፅዋት እና እንስሳት መገኛም ነው::
ለደኑ ጥብቃና ዘላቂነት የእረሻ መሬት ለማስፋፋት የደን መመንጠር፣ ልቅ ግጦሽ እና የደን ቃጠሎ ስጋት መሆናቸውን ድረ ገፆች አስነብበዋል::
ለዘገባችን በመረጃ ምንጭነት ሪስፖንስብል ትራቭል ድረ ገጽ፣ ኦንላይን ላይብራሪ ዊሊ ድረገፆችን እና ጐግልን ተጠቅመናል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የካቲት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም


