ማስተዋወቅን ዓላማ ያደረገዉ  ውድድር

0
61

በቻይና ዠጂያንግ ግዛት “ዩኒትሪ” የተሰኘው ኩባንያ “ጂ1” በሚል ስያሜ ያመረታቸውን ሮቦቶች ዓቅማቸውን በማሳየት ማስተዋወቅን ዓልሞ ለመጀመሪያ ጊዜ ያዘጋጀው ውድድር በብዙሃን መገናኛዎች መሠራጨቱን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ ለንባብ አብቅቶታል::

ሮቦት አምራቹ ኩባንያ “ዩኒትሪ” በዠጂያን ግዛት ያዘጋጀው ልዩ የካራቴ እና የቦክስ /የኪክ ቦክሲንግ/ ውድድር “ጂ1” የተሰኙ የሮቦት ምርቶቹን ብቃት ለማስተዋወቅ ያለመ ነው:: በውድድሩ የተሳተፉት “ጂ1” ሮቦቶች አንድ ሜትር ከሰላሳ ሴንቲ ሜትር ቁመት እና 35 ኪሎ ግራም ክብደት ያላቸው መሆኑም ተገልጿል::

 

በቻይና መንግሥት ባለቤትነት በሚተዳደረው ቻይና ሴንትራል ቴሌቪዥንም (ሲሲቲቪ) በቀጥታ ስርጭት ለእይታ በቅቷል- ውድድሩ:: በመክፈቻው ኘሮግራም አራት “ጂ1” ሮቦቶች ጥንድ ጥንድ ሆነው በመወዳደሪያ ቀለበት ውስጥ ገብተው ተጋጥመዋል::

የሮቦቶቹ ፍልሚያ በሰው ዳኛ  ክትትል፣ ህግ እና ደንብን ማስከበር እንዲሁም ለረዢም ደቂቃ ሲያያዙ ወይም ታቃቅፈው ሲቆዩ የማለያየት ተግባርም ተከውኗል::

ተወዳዳሪዎቹ ሮቦቶች በውድድሩ መጀመሪያ የጭንቅላት መከላከያ፣ ደረጃውን የጠበቀ የቦክስ ጓንት ማድረጋቸው ተረጋግጧል- በዳኛው:: በግጥሚያ ተመቶ የወደቀ ሮቦት በወደቀበት ስምንት ሰከንድ  ሲቆጠር ካልተነሳ በዝረራ መሸነፉን ዳኛው በምልክት ያሳዩበት ትርኢትም ነበር::

 

የሮቦቾቹ የፍልሚያ እንቅስቃሴ በርቀት መቆጣጠሪያ መሣሪያ እና የድምፅ ትእዛዝን በሚያቀናጁ ከውድድር ቀለበቱ ውጪ ባሉ ባለሙያዎች ጭምር ነው የተመራው::

የመጀመሪያዎቹ ሁለት ውድድሮች ተካሂደው አሸናፊዎቹ ከተለዩ በኋላ የየጥንዱ አሸናፊዎች የመጨረሻ ለአሸናፊዎች አሸናፊነት ተፋልመዋል::

በመጨረሻም “ዩኒትሪ” የተሰኘው ኩባንያ በውድድሩ ያቀረበው  ሮቦት በፍልሚያው በነጥብ የበላይነት አግኝቶ  ለአሸናፊነት መብቃቱን  ድረ ገጹ አስነብቧል::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር የሰኔ 2 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here