የተስተካከለ እንቅልፍ የማይወስዳቸው ሰዎች አንጐላቸውን ከትክክለኛው እድሜ የበለጠ በማስረጀት የማገናዘብ አቅማቸውን እንደሚቀንስው ሳይንስ ዴይሊ ድረ ገጽ ሰሞኑን ለንባብ አብቅቶታል::
በስዊዲን የካሮሊንስካ የጤና ተቋም ተመራማሪዎች ቡድን መሪ አቢጋይ ዶቭ ከአንድ ሺህ የሚበልጡ የሰዎች አንጐል በ (ኤም አርአይ) የተነሳን ምስል መሰረት አድርገው ምርምር አድርገዋል:: የጥናቱ ተሣታፊዎች በሦስት ቡድን ተከፍለው ጤናማ አራት፣ መካከለኛ ከሁለት እስከ ሦስት፤ ደካማ- አንድ ነጥብ ተሰጥቷቸው የእንቅልፍ ሁኔታቸው ደረጃ ወጥቶለታል:: የእንቅልፍ ጥራት ጊዜው ቀን ወይም ማታ መሆኑ፣ በማንኮራፋት የሚያልፍ ጊዜ ወዘተን አካተው ገምግመዋል- ከናሙና ተሣታፊዎቹ::
ተመራማሪዎቹ ናሙና ጥናት ካደረጉበት የ “ኤም አርአይ” ምስል በመነሳት የእንቅልፍ ባህሪያት እና ከአንጐል እድሜ ጋር ያለውን ተዛምዶም በትኩረት ፈትሸዋል:: የተሣታፊዎችን ቁጥር በማሳደግ በጥልቀት ገምግመውም ደካማ እንቅልፍ የአንጐል እርጅናን እንደሚያፋጥነው ነው የደረሱበት -ተመራማሪዎቹ::
የተስተካከለ እንቅልፍን ማስፈን የሚቻል መሆኑን ያሰመሩበት የተመራማሪዎቹ የቡድን መሪ በዚህም የተፋጠነ የአንጐል እርጅናን እና የግንዛቤ ማሽቆልቆልን በጤናማ እንቅልፍ መከላከል እንደሚቻልም ነው የጠቆሙት::
የጤና ችግሩን እና መፍትሄ ያሉትን በበለጠ ሲያብራሩም ደካማ እንቅልፍ በአንጐል ውስጥ የሚፈጠር ቆሻሻ እና በአወጋገድ ስርዓቱ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያሳርፋል::
እንቅልፍ ውስብስብ የአንጐል ሂደት መሆኑን የጠቆሙት ተመራማሪዎቹ በነጠላ መለኪያ ሙሉ በሙሉ ወደ ሚፈለገው እውነታ መቅረብ እንጂ በእርግጠኝነት ሙሉ በሙሉ የሚፈለገው መረጃ ላይ እንደማያደርስም ነው ያሰመሩበት:::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የጥቅምት 3 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም