ዴይፎረስት ብሔራዊ ፓርክ በጅቡቲ ሰሜናዊ ቀጣና በጐዳ ተራሮች እና ታጁራ ክልል ነው የሚገኘው:: አገሪቱ ካሏት ሁለት ፓርኮች በስፋቱ ቀዳሚ ነው:: አጠቃላይ ስፋቱም 15 ኪሎ ሜትር ስኩዌር ተለክቷል:: የምስረታ ጊዜውም በ1939 እ.አ.አ ነው::
ከጅቡቲ ከተማ ወደ ብሔራዊ ፓርኩ ለመድረስ በተሽከርካሪ 60 ኪሎ ሜትር፤ ለሁለት ሰዓት መጓዝን ግድ ይላል::
በፓርኩ ቀጣና የሚገኘው ደን አገሪቱ ካላት የደንሽፋን አብዛኛውን በመያዙ ተጠቃሽ ቢሆንም በዓለማችን በደን ሽፋን አነስተኛ መጠን ካላቸው አገራት መካከል ነው የምትመደበው- ጅቡቲ::
ፓርኩ በሰሜናዊ አፍሪካ ወይም ከሳሀራ በላይ ቀደም ባሉት ክፍለ ዘመናት ከነበረው እና ከውድመት የተረፈ የጥድ፣ የዱር ወይራ፣ እና የቁጥቋጦዎች መገኛ ነው:: በፓርኩ ከዱር እንስሳት ዝንጀሮ እና የሜዳ ፍየል፣ ከተሳቢ እንስሳት እባብ እና የተለያዩ የሞቃት ቀጣና የእንሽላሊት ዝርያዎች ይገኙበታል::
ከዓዕዋፍ በአገሪቱ የሚታወቁት “ፍራንኮሊን” የተሰኙ ዝርያዎች በብዛት ይገኛሉ:: በተጨማሪም ባለ አረንጓዴ ክንፍ ፒቲሊያ እና ፍላይካቸርንም አቅፏል::
ፓርኩን ለመጐብኘት ሙቀቱ በማያይልበት መጠነኛ ዝናብ በሚጥልበት ከጥቅምት እስከ ሚያዚያ ያሉት ወራት ተመራጭ መሆናቸውን ድረ ገፆች አስነብበዋል::
ከየትኛውም ቦታ ወደ ፓርኩ ለሚያቀኑ ጐብኚዎች በዋና ከተማዋ ጅቡቲ ወይም ቡታጁራ ከተማ ባናዲር ሆቴል እና የጅቡቲ ቤተመንግሥት “ኬምፒንስኪ” የተሰኙ ለማረፊያነት ዝግጁ ሆነው እንደሚጠባበቁ ድረገፆች አስነብበዋል::
ለዘገባችን በመረጃ ምንጭነት ናሽናል ፓርክ አሶሴሽን፣ ዋይልደርነስ ኤክስፕሎር አፍሪካ፣ ዋይልደርንስ አፍሪካ እና ዋኪፒዲያ ድረ ገፆችን ተጠቅመናል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የህዳር 1 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም


