ከባድ የሚጥል በሽታ ላለባቸው ልጆች ዘረመል ላይ ተመስርቶ በምርምር የተገኘ “ዞሬቨነርሰን” የተሰኘ መድሃኒት የበሽታውን ድግግሞሽ 91 በመቶ በመቀነስ የታካሚዎቹን ጤንነት ማሻሻሉን ሳይንስ ዴይሊ ድረ ገጽ ሰሞኑን አስነብቧል::
የለንደን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በመረጃ ምንጭነት ለህትመት እንዳበቃው ከተለያዩ ተቋማት በተውጣጡ ተመራማሪዎች የተገኘው መድሃኒት የሚጥል በሽታ የሚከሰትበትን ድግግሞሽ 91 በመቶ መቀነስ አስችሏል::
ከባድ የሚጥል በሽታ የተለያዩ የእለት ተእለት የእንቅስቃሴ ችግሮችን ከማስከተል ባለፈ ለሞት የሚያበቃ መሆኑም ነው የተገለፀው፤ ከዚህ በፊት ለችግሩ መፍትሄ አለመገኘቱንም ጠቁመዋል- ተመራማሪዎቹ::
የጤና ችግሩ መንስኤ ለሰዎች ከሚያስፈልጉ ሁለት የፕሮቲን ዓይነቶች አንዱ በበቂ መጠን አለመመረቱ መሆኑን የተገነዘቡት ተመራማሪዎቹ ለጤናማ የነርቭ ስርዓት አስፈላጊ የሆነው ፕሮቲን በበቂ መጠን እንዲመረት የሚያስችል መድሃኒት ነው ያዘጋጁት::
መድሃኒቱ ከሁለት እስከ አስራ ስምንት ዓመት እድሜ መካከል ለሚገኙ የጤና ችግሩ ላለባቸው ልጆች ተሰጥቷቸው ውጤቱ መመዝገቡንም አረጋግጠዋል- ተመራማሪዎቹ::
በለንደን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የምርምሩ መሪ ኘሮፌሰር ሄለን ክሮስ፣ የህፃናት የነርቭ ህክምና የክብር አማካሪ አዲሱ መድሃኒት ለከባድ የሚጥል በሽታ የተዳረጉ ልጆችን ጤና በማሻሻል ደስተኛ ህይወት እንዲመሩ ማስቻሉን ገልጸዋል::
ፕሮፌሰር ሄለን ክሮስ የአዲሱ መድሃኒት ግኝት ሁለት ደረጃዎችን ማለፉን እና አሁን ባለበት ለመጨረሻ (ሦስተኛ) ደረጃ ግምገማ መቅረቡን አስታውቀዋል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የመጋቢት 7 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም


