ክሩገር ብሔራዊ ፓርክ በደቡብ አፍሪካ ከዋና ከተማዋ ጆሀንስበርግ በግምት ከ400 እስከ 500 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ነው የሚገኘው:: የፓርኩ ስፋትም 19 ሺህ 485 ኪሎ ሜትር ስከዌር ተለክቷል::
ፓርኩ አገሪቱ ካሏት ዘጠኝ ግዛቶች በሁለቱ ሊምፖፖ እና ማፑ ማላንጋ ውስጥ የተካለለ ነው:: አብዛኛው የፓርኩ ቀጣና መገኛ ከባህር ወለል በላይ በምሥራቅ 200 ሜትር እስከ ደቡብ ምዕራብ 840 ሜተር ከፍታ ያለው መሆኑም ተለክቷል::
በፓርኩ ከእፅዋት 400 ዝርያዎች መኖራቸው ተረግግጧል:: ሳር ለበስ ሜዳ እና ደን የመልካ ምድሩ ገጽታ አካል ናቸው::
ከዱር እንስሳት 147 የአጥቢ እንስሳት ዝርያዎች፣ 114 የተሳቢ እንስሳት፣ 49 የአሳ እና 34 በውኃ እና በየብስ የሚኖሩ “አምፊቢያንስ” ዝርያዎች መገኘታቸውን ድረ ገፆች አስፍረዋል::
በአካል መጠን ግዝፈት ካላቸው አውራሪስ፣ ዝሆን፣ ጉማሬ፣ አንበሳ፣ አቦሸማኔ፣ የሜደ አህያ፣ ቀጭኔ፣ የሜዳ ፍየል፣ ዓዞ እንደሚገኙ ነው የሰፈረው- በድረ ገፆች:: የእያንዳንዳቸው ብዛት ከተጠቆሙት 1 ሺህ 500 አንበሶች፣ 12 ሺህ ዝሆን፣ 2 ሺህ 500 ጐሽ፣ 1 ሺህ አቦ ሸሜኔ እና 5 ሺህ አውራሪስ እንደሚገኙ ባለሙያዎች ግምታቸውን አስፍረዋል::
በፓርኩ ቀጣና እንደየጐብኚዎች ፍላጐት እና ምርጫ ሆቴሎች፣ የእንግዳ ማረፊያዎች ተዘጋጅተዋል::
ወደ ፓርኩ በተሽከርካሪ ኮጆሀንስበርግ፤ በአውሮኘላን ኮጀርጅ ወይም ኤልዛቤት አየር ማረፊያ በጆሀንስበርግ ወይም ከደርባን ወደ ክሩገር ማፑ ማላንጋ አየር ማረፊያ መድረስ ይቻላል::
ለፓርኩ ዘላቂነት ከቀጣናው ውጪ የመጡ ለውኃ እጥረት የሚዳረጉ መጤ ዝርያዎች ስጋት መሆናቸውም ተጠቅሷል::
ለዘገባችን በመረጃ ምን ምንጭነት ስቶሪ ኦፍ ክሩገር፣ ክሩገር ናሽናል ፓርክ እና ሳንፓርክ ዶት ኦርግ ድረ ገፆችን ተጠቅመናል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የመጋቢት 21 ቀን 2018 ዓ.ም ዕትም


