የ65 ዓመቱ ኬ ፓድማራጃን ላለፉት 30 ዓመታት በተካሄዱ ምርጫዎች 238 ጊዜ ተሳትፎ ቢሸነፍም በ2024 ተስፋ ሳይቆርጥ ለወረዳ የፓርላማ ተወካይነት ለመወዳደር በዝግጅት ላይ መሆኑን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ አስንብቧል::
“የምርጫ ንጉሥ” ወይም “በዓለም በምርጫ ተሸናፊነት ቁንጮ” የሚል ቅፅል ስም የተሰጠው ተስፋ የማይቆርጠው ህንዳዊ ባለፉት 30 ዓመታት በምርጫ ለመወዳደር በርካታ ገንዘብ ማውጣቱ ተገልጿል::
ኬ ፓድማራጃን ለአሸናፊነት ተቃርቦ የነበረው በ2011 እ.አ.አ ነበር:: ከአሸናፊው ተከታይ ድምፅ ያገኘበት፤ ይኽው ዓመት እስከ ህይወቱ ፍፃሜ ተስፋ መቆረጥ እንደማይኖርበት ፅናትን አስተምሮታል:: እናም አንድ ቀን እንደሚሳካለት ዕምነቱ መሆኑን ነው የተናገረው::
ፓድማራጃን በምርጫ መሣተፍ የጀመረው በ1998 እ.አ.አ ለትውልድ ከተማው ሜትቱር በመወዳዳር ነበር:: ያንጊዜ ሲወዳደርም እንደማያሸንፍ ያውቅ እንደነበር ነው በድረ ገጹ የተገለፀው:: ዓላማው ግን ማንኛውም ሰው በግልፅ የመወዳደር መብት ያለው መሆኑን በአርዓያነት ማመላከት እንደነበረ ነው ያስረዳው::
ባለፉት 30 ዓመታት የምርጫ ውድድር ተሣትፎው በህንድ ታዋቂ ጠቅላይ ሚንስትር በነበሩት እንደ ናራንድራ ሞዲ፣ አታል ቢሀሪ ቪጂፓይ እና ማን ሞሀን ሲንግ በመሳሰሉቱ ተሸንፏል:: በቃ ሽንፈቱን ተቀብሎ በዘንድሮው 2024 እ.አ.አ ለ239ኛ ጊዜ ምርጫ ለመወዳደር ተዘጋጅቷል::
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር ሚያዚያ 7 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም