የነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክ

0
269

ነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክ በደቡብ ክልል፣ ከአዲስ አበባ 510 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በአርባ ምንጭ ከተማ አቅራቢያ በአባያ እና ጫሞ ሀይቆች መካከል ይገኛል::

ፓርኩ በ1979 እ.አ.አ  በዓለም አቀፉ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ህብረት ነው የተመሰረተው:: በሁለቱ ሀይቆች መካከል የእግዜር ድልድይ ተብሎ የሚጠራ የተንጣለለ የመሬት ወሽመጥ ላይ የተከለለ ፓርክ ነው:: የፓርኩ ክልል 514 ኪሎ ሜትር ስኩዌር ወይም 127 ሺህ ሄክታር ተለክቷል::

ፓርኩ ከመሬት ወለል በላይ ከ1 ሺህ 250 እስከ 1 ሺህ 650 ሜትር ከፍታ ልዩነት ተመዝግቦበታል:: ፓርኩ በከፍታ እስከ 4 ሺህ ሜትር የተለካዉ  የሲዳሞ ተራራ መገኛም ነው::

የፓርኩ ክልል ደን፣ የከርሠ ምድር ውኃ፣ የተፈጥሮ ፍል ውሀ እና በሣር የተሸፈነ ሜዳን ያካተተ ነው:: ስነ ምህዳሩ በበርካታ አጥቢ እንስሳት፣ በዓሳ እና በእጽዋት ዝርያዎች መኖሪያነቱም ይታወቃል::

በፓርኩ ውስጥ ከሚገኙ አጥቢ እንስሳት አንበሳ፣ ጉማሬ፣ የሜዳ አህያ፣ ጦጣ፣ ጅብ ወዘተ ይገኙበታል:: አእዋፍትን በተመለከተም ከ300 በላይ ዝርያዎች ተመዝግበዋል:: በሀይቆቹ እና ወንዞች “ናይል ፐርች” ዓሳዎች በብዛት እንደሚገኙ ድረ ገጾች አስነብበዋል:: ሀይቆቹ በርከት ያሉ ዓዞዎች መናኸሪያ ሲሆኑ እስከ ስምንት ሜትር የሚረዝሙ ዓዞዎች መገኘታቸውን የድረ ገጾች ጽሑፍ አመላክቷል:: በተጨማሪም በአባያ ሀይቅ ዳርቻ የአዞ ገበያ መኖሩ ነው የተገለፀው::

በፓርኩ ክልል ከሚገኙ እጽዋት በርከት ብለው ግራር፣  በለስ በየሳሩ እና ኮረብታዎች መካከል ይታያሉ:: የእጽዋት ዝርያ ከቦታ ቦታ እንደየወቅቶቹ ሳስቶ እና ተበራክቶ ነው የሚስተዋለው- በፓርኩ ክልል:: ይህም በወቅቶቹ የዝናብ፣ የሙቀት መጠን ወዘተ. ለልዩነቶቹ  ምክንያት መሆኑን ልብ ይሏል::

በሀይቆቹ መካከል የተንጣለለው የነጭ ሳር ሜዳ በግልቡ ሲያዩት ባዶ ይመስላል:: ነገር ግን በትኩረት ለተመለከተ የሜዳ አህያ መንጋ፣ ቀበሮ፣ የዱር ውሻ “ስዋይን ሀርት ቢስት” ለዕይታው  ይበቃሉ::

የነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክን በከበቡት ሀይቆች ዳርቻ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ አስራ አምስት የቢራቢሮ እና ስምንት የውኃ ተርብ ዝርያዎችንም ይዟል::

ለዘገባችን አክሸንተር ኢትዮጵያ ሜክ ሄሪቴጅ ፈን፣ እና ኢትዮቪዚት ድረ ገጾችን ተጠቅመናል::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር ሚያዝያ 21 ቀን 2016 ዓ.ም ዕትም

 

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here