በህንድ ቼንጋልፓቱ ወረዳ ቲሩፓሩር በሚገኘው ቤተመቅደስ መባ ወይም ስጦታ መሰብሰቢያ ሳጥን ውስጥ የሞባይል ስልኩ ወድቆበት እንዲመለስለት ለጠየቀው አማኝ በማንኛውም ጊዜ እና ሁኔታ መመለስ እንደማይቻል የተነገረው መሆኑን ኤንዲቲቪ ድረ ገጽ ሰሞኑን አስነብቧል፡፡
ባለፈው ታህሳስ ወር መጨረሻ ከቤተሰቡ ጋር የሂንዱ ቤተመቅደስን እየጐበኘ የነበረ ሰው በአጋጣሚ አይፎን የሞባይል ስልኩ ከኪሱ ሾልኮ በችሮታ መሰብሰቢያ ሳጥን ውስጥ ይወድቅበታል፡፡ ግለሰቡ ለቤተመቅደሱ ኃላፊዎች ቀርቦ ሞባይል ስልኩ እንዲመለስለት ሁኔታውን ቢያስረዳም በፈቃደኝነትም ሆነ በድንገት በስጦታ መሰብሰቢያ ሳጥን የወደቀ ንብረት እንዲመለስ ህጉ እንደማይፈቅድላቸው ነው ምላሽ የሰጡት፡፡
ተስፋ ያልቆረጠው “ዳኒሽ” በሚል ስም የሚጠራው ግለሰብ ለሂንዱ ሀይማኖት እና የበጐ አድራጐት ሃላፊዎች ቅሬታውን በማቅረብ ሳጥኑ የሚከፈትበትን ቀን ጠብቆ ቢጠይቅም፣ ንብረቱን ማግኘት አለመቻሉን በመሬት አስረድቷል፡፡
የሂንዱ ሀይማኖታዊ እና የበጐ አድራጐት ስጦታዎች ክፍል ሚኒስትር ሴካርባቡ በበኩላቸው ለቀረበላቸው የግለሰቡ ጥያቄ በሰጡት መልስ መባ ሳጥን ውስጥ የተቀመጠ ማንኛውም ነገር ወይም ቁስ ባለማወቅ የተደረገም ቢሆን ንብረትነቱ የቤተመቅደሱ መሆኑን ነው አስረግጠው የተናገሩት፡፡
የመጨረሻ የማይሻር ውሳኔያቸውን ያስታወቁት የበላይ ኃላፊው ግለሰቡ ከፈለገ በአይፎን የእጅ ስልኩ ላይ የሚገኘውን መረጃ ብቻ ሊሰጡት እንደሚችሉ ነው ያስታወቁት፡፡
(ታምራት ሲሳይ)
በኲር የጥር 5 ቀን 2017 ዓ.ም ዕትም