ግዙፉ የተሽከርካሪዎች ማጓጓዣ

0
104

በዓለማችን 9100 ባለ አራት ጐማ ተሽከርካሪዎችን ጭኖ የማጓጓዝ ዓቅም ያለው መርከብ ቀደም ብሎ 8500 በመጫን አንደኛ የነበረውን በልጦ ቀዳሚ ሊሆን መቻሉን ኦዲቲ ሴንትራል ድረ ገጽ ሰሞኑን ለንባብ አብቅቶታል::

በቻይና ጂያንግዙ ከባድ ተሽከርካሪ ማምረቻ ኢንዱስትሪ በ2024 እ.አ.አ ነው የተመረተው -የተሽከርካሪ ማጓጓዥ መርከቡ፤ የጐን ስፋቱ 37 ነጥብ 5፣ ርዝመቱ  ደግሞ 200 ሜትር ተለክቷል::

የመረከቡ ስሪት ጠንካራ እንዲሆን የተጠበቡበት መሀንዲሶች በ14ቱም ወለሎች ተሽከርካሪዎችን የመሸከም ዓቅም አጐልብተውለታል:: የግዙፉ መርከብ አስደናቂነቱ የጭነት ልኩ ብቻ ሳይሆን ለአካባቢ ተስማሚ ማለትም ከባቢ ዓየርን የመበከል ደረጃው በእጅጉ ያነሱ መሆኑ በዋናነት ተጠቁሟል::  ለዚህ ደግሞ በመርከቡ የላይኛው ክፍል 1500 ካሬ ሜትር ስፋት ካለው የፀሀይ ሃይል መሰብሰቢያ ንጣፍ የሚገኝ ከብክለት የፀዳ ኃይልን ለመንቀሳቀሻ ማዋሉ በውጤትነት ተጠቅሷል::

ግዙፉ የተሽከርካሪ ማጓጓዣ መርከብ አሁን ላይ ከፀሃይ ብርሃን ከ30 እስከ 35 በመቶ ኃይል በመሰብሰብ ተለምዷዊውን ከብስባሽ የሚገኝ ነዳጅ  መተካት ችሏል::

የጭነት ማጓጓዣ መርከቦች ድርጅቱ “ሆግ አውቶ ላይነርስ” የበላይ ኃላፊ ሰብጆርን ዳሀል ድርጅታቸው በቀጣይ መርከቦቹን ሙሉ በሙሉ ከብክለት በፀዳ ኃይል ለማንቀሳቀስ ማቀዱን አስታውቀዋል::

ለዚህም በድረጅታቸው ውስጥ ያሉትን 12 ግዙፍ መርከቦች በ2027 እ.አ.አ የካርበን ልቀታቸውን ዜሮ ለማድረስ ተግተው እየሰሩ መሆናቸውን ነው ያሰመሩበት::

በባህር ማጓጓዣ ዘርፍ የሚሰሩ በርካታ ግዙፍ ድርጅቶች መኖራቸውን የጠቆሙት ኃላፊው በተናጠል ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ጋርም በመተባበር እና በመቀናጀት የድርጅቶቹ ማጓጓዣዎች ሙሉ በሙሉ ከበካይ ልቀት ነፃ እንዲሆኑ እንደሚሰሩ ነው ቃል የገቡት::

(ታምራት ሲሳይ)

በኲር የመጋቢት 8 ቀን 2017 ዓ.ም  ዕትም

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here